Friday, October 25, 2013

ጫልቱ እንደ ሄለን ከቡርቃ ዝምታ የቀጠለው መርዛማ ብዕር

October 24, 2013

ዳኛቸው ቢያድግልኝ
ተራሮች አንቀጠቀጥኩ ያለው ትውልድ አካል ነኝ ባዩ ወንድማችን በቡርቃ ዝምታው በማር የተለወሰ መርዝ አሰናድቶ አማራና ኦሮሞ ሲተራረድ ዙርያ ከበው በለው! አትማረው! የሚሉትን የአባቱን ሀገር ፖለቲከኞች አስቦ የጻፈው ክታብ መሆኑ ተነግሮ አብቅቶለታል። ተስፋዬ የጦር ሜዳ ዘጋቢነቱን በኢትዮጵያውያን ተምሮ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ብለው ለሚወጉን ማገልገሉና በደል መፈጸሙ እውነት ነው። ለዚህ ውለታውም የዘመናት ታሪክ ያለውን ድርጅት ያለምንም ክህሎት በአዛዥነት ይዞ እንዳሻው እንዲፈነጭበት ተሰጥቶት ነበር። ቁንጮ ሆኖም የሚበቃውን መረጃ ከክምችቱ እንዲያገኝ ሆኖ መሰየሙንና ክምችቱንም ለፕሮፓጋንዳ መሳርያነት እንዲጠቀምበት ሙሉ መብት ተሰጥቶት እንደነበረም እናውቃለን። ተስፋዬ አገር የለቀቀበትን ጊዜ መለስ ብለን ብንመለከት ለሻዕብያ ያለው ቅርበት ከወያኔ ጋር ለመቀያየም ምክንያቱ መሆኑን መገመት ይቻላል። በተስፋዬ ስራዎች ውስጥ የኤርትራ ጉዳይ ልዩ ቦታ እንዳለውና ከጻፈም ጀግና ብልህና አስተዋይ እንደሚያደርጋቸው የታወቀ ነው።Tesfaye Gebreab's New Book: “Yesidetegnaw Mastawesha
ስለዚህ ኤርትራዊነት አያደላበትም ወይም ለኤርትራ መረጃ አያቀብልም ብሎ ያለመገመት ከመነሻው የሚገርም ጉዳይ ነው። በቅርብ ድርሰቶቹ ወያኔዎቹን በተመለከተ የአሉባልታ ዶፍ ማውረዱና ይልቁንም ዱላው የጠነከረው ለሻዕብያ ወገንተኛ አይደሉም ባላቸው ላይ መሆኑም የሚያመለክተው ይህንኑ ነው። በማሩ ቃላት አሉባልታዎች ከመገለጻቸው በቀር የፖለቲካ ፋይዳ ያላቸው የማይታወቁ ድብቅ ምስጢሮች የሚባሉ ነገሮችም የሉበትም። ስለዚህ ተሥፋዬ የት እንደሰፈረ የሚሸሽግ አንዳች ነገር ከሌለ ፈቅደን የታለልንለት ድንገት መባነናችንና ምስጢሩ እንደተገኘ ያለማሳወቃችን ለምን በዚህ ጊዜ ሆነ ብለው ለሚጠይቁ ጠርጣሪዎችም የውይይት ማንደርደርያ ቢሆን አይገርምም። የአብርሃ ደስታን ምልከታ እጋራዋለሁ። የተሰጡ አስተያየቶችን አንብቤያለሁ። ጥሩ የሚባል ነገር ሲጻፍ ማመስገን ስህተት ሲኖርም ስህተት እንደመጠቆም የዘር ሀረግ ላይ ተንጠልጥሎ መራገም ውይይታችንን ጤናማ ያደርገዋል የሚል እምነት የለኝም። የቀረበበት ማስረጃ ግን አንዳንድ የዋሆች ለኦሮሞ ካለው ፍቅርና አክብሮት አንጻር የተንገበገበ ሳይሆን የእልቂት ድግሳችንን እያጧጧፈ እንደሆነ እንዲገነዘቡ ያደርጋል ብዬ አምናለሁ።
ተስፋዬ የቢሾፍቱ ልጅ ነው ሥጋና ደሙን የቢሾፍቱ አፈርና ወሀ ገንብተውለታል፣ አንደበቱን የገራለት ሀሳቡን በዚህ መልክ ይገልጥበት ዘንድም የቋንቋ ቁልፉን ያስጨበጠው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው። ይሁን እንጂ ወንድማችን ተሥፋዬም የማንነት መምታታት የማያውቀውን አገር የመናፈቅ ግራ መጋባት ውስጥ አይደለም ብዬ አልገምትም። ከጠባው ጡት ጋር ሲነገረው የኖረ የጥላቻ መርዝ መኖሩንም በጻፈው ማስታወሻ ላይ  ግልጽ ብሎ ተቀምጧል። አብሮ አደጎቹን ወይም በስደት ዘመን ያገኛቸውን ሁሉ ለዚህ የፖለቲካ ጥቅም በቢሾፍቱ አድባር ስም እየማለ ሊጠቀምባቸው ቢሞክር አይደንቅም። እንዲያውም ለአባት አገሬ አደረኩ የሚለውን እያሰበ በበግነታቸው ድዳቸውን ማስገልፈጡንና የበግ ነጋዴነቱ ውስጡን ያስቁት ያኩራሩትም ይሆናል። “በግ እሰራ” ነበር ማለቱ ድንገት የተጻፈች አረፍተ ነገር ናት ብሎ ማሰብ እንዲከብደን ሆኗልና። እንዲያም ሆኖ ወንድማችን ያለኢትዮጵያዊነት ነብሱ ባዶ መሆንዋን አልጠራጠርም። ከኢትዮጵያ ሌላ ባማረ አማርኛ ለማንስ ሊጽፍ ይቻለዋል?  በሁለት ባላ ላይ ለተንጠለጠለቺው ነብሱ በጣም አዝናለሁ። የአባቱን ሀገር ለማገልገል ቆርጦ የተነሳ ቢሆንም እንደ ተበላ ሰላይ ሜዳ መውደቂያውን ማፍጠኑ ግን ብልህነት እንደሚያንሰው ያሳያል።
ለዚህም ይሆናል የስደተኛው ማስታወሻ በወቅቱ ከሕዝቡ ጆሮ ካልገባ የሚያመጣው የፖለቲካ ትርፍ ስለሚቀንስ በነጻ እንድናነበው የሆነው። እኔም ገረፍ ገረፍ አደረኩት ማለትም ለመተቸት በሚያስችል መጠን አልተመለከትኩትም። ብቻ ዘመን አቆጣጠሩን ‘በግዕዝ’ የሚል ሲቀጥልበት እንደ ኢትዮጵያ ማለት ከብዶት ይሆን? ብዬ ማሰቤ አልቀረም። በጠቅላላው ዘረፍ ዘረፍ የሚያደርጋቸው ቃላትና ጠቅለል አድርጎ የሚገልጽባቸው አረፍተ ነገሮች በውል ሊታዩ የሚገባ ነው። ሳይንሱን ባለመረዳቱ ስለፍጥረት የሚሰጠው ምሳሌም የሚተች ነው። ጦስኝ ሳር አይደለም የበግ ሽንትም ሳር ማስተኛቱን እጠራጠራለሁ። ምናልባት የቢሾፍቱ በጎች ከሆራው እየጠጡ እንደ እሳት አደጋ ጎርፍ ይሸኑ አንደሆን አላውቅም።
ሌላው ምሳሌ አንበጣ ብሎ የጻፈው ስለ ምስጥ ነው። አንበጣማ ከፊቱ ያለውን እየጠረገ ጥቁር ደመና መስሎ  ብዙ ኪሎሜትሮችን ያካልላል። ምስጥ ክንፍ የሚያወጣው ሩቅ ለመብረር አቅዶ አይደለም እንደ ተስፋዬ ግምትም ክንፋቸው ሲረግፍ ባጭር መቅረታቸው አይደለም። የምስጥ ንግስትና ንጉስን ለመፍጠር ከተለያየ መኖርያ ቤታቸው (ኔስት) በተመሳሳይ ጊዜ ወጥተው ወንድና ሴት የሚፈላለጉበት ተፈጥሮ የምትደግሰው ድንቅ ሰርግ ነው። ጋብቻ ካንድ ቤተሰብ እንዳይሆን የዚህኛው ቤት ልጃገረድ ምስጥ ከዚያኛው ቤት ኮበሌ ጋር ዝናብ ሲያባራና አመሻሹ ላይ እየበረሩ ትንሽ ይዳራሉ። ወንድየው ሴቲቱን ተጠግቶ “ሁኚኝ” ይላታል ከፈቀደች ትሆነዋለች። ያኔ ፍቅር መስራት ይጀምራሉ፣ ክንፋቸውን አራግፈውም ጎጆ ለመቀለስ የክረምቱ ዝናብ ያለሰለሰውን አፈር ማስ ማስ አድርገው ሃኒሙን ይጀምራሉ። የነርሱን ጋብቻ ደግሞ የእረኞች የቡሄ ጅራፍ ያደምቀዋል። ተስፋዬ ይህን አውቆ ቢሆን ባማሩ ቃላት ወሲብ ወሲብ እያሰሸተተው ይህንን ጋብቻ ለመፈጸም ከየጉድጓዱ እየወጡ ከወፎች አደን ተርፈው አዲስ ጎጆ የሚቀልሱትን የህይወት ታሪክ በጻፈው ነበር። ንግስቲቱ በቀን ከሺህ በላይ እንቁላል እየጣለች በሰራተኛና በወታደር የታጀበ መንግስት እንደምታቋቁምና ኩይሳ የምንለውን ከኢንጅነሮች ሙያ የላቀውን ቤተመንግስትም እንደምታስገነባና ሌላም ሌላም በነገረን ነበር። ያወቅን የሚመስለን ብዙ የማናውቀው የተፈጥሮ ምስጢር ቢገለጽልን ኖሮ እርስበርስ ለመጠፋፋት ጦር ባላመዘዝን ነበር። ሆኖ ያለፈን ነገር ወይም እየሆነ ያለን ስህተት በቅንነት ተነጋግረን አብሮነታችንን ማስዋብ የሚቸግረን አይደለንምና ወዳጅ መስለው መርዝ የሚረጩትን ማጋለጥ ተገቢ ነው።
ስለ አንድ የሶማሌ ህጻን እሱን አይቶ ማልቀስ ሲጽፍ ይህ የሶማልያ ህፃን እኔን ሲመለከት ለምን እንዳለቀሰ ማሰላሰል ያዝኩ… “አበሻ እባብ” እንደሚለው ነባር የሶማሌ ብሂል እባብ መስዬ ታይቻቸው ይሆን…. የሚል መንደርደርያ ከጻፈ በሁዋላ ወረድ ብሎ ደግሞ በብዙ አለም አቀፍ ሚዲያዎች ኢትዮጵያ የኤርትራና የሶማሌ ጠላት እንደሆኑ ይነገራል ይለናል ይህንን ቅጥፈት ካስነበበ በሁዋላ ደግሞ እባብ ስለመግደሉ ሲነግረን እግዚአብሄር.. የእባብን አናት ቀጥቅጠህ ትገድለዋለህ ሲል ያዘዘውን እኔ በተደጋጋሚ ፈጽሜዋለሁ የፈጣሪን ቃል በማክበር ረገድ በተሟሉ ሁኔታዎች ተሳኩልኝ ብዬ ከምኮራባቸው ትዕዛዛት ዋናው “የእባብን ጭንቅላት ቀጥቅጡ” የተባለው ሳይሆን አይቀርም በሚል ይደመድመዋል። እነዚህ በተን ተደርገው የተረጩት በመጀመርያ አበሻና እባብ ከዚያ አበሻ የሶማሌና የ ኤርትራ ጠላት በመጨረሻም አግዜር እባብን ቀጥቅጡ ባለው መሰረት እባብ መቀጥቀጥ ተሳክቶልኛል የሚሉ እንደ እባብ ቃላት ውስጥ እየተሹለከለኩ የሚሄዱ መርዘኛ መልዕክቶቹን አስፍሮበታል። መጽሃፉን ለመተቸት ሳይሆን አንዲት በየምዕራፎች ተብትና የተቀመጠችውን ስራውን በተመለከተ ብቻ ጥቂት ለማለት ነው። ሌሎቹ ዋናው ተልዕኮአቸው ማዳመቅ ይመስለኛል።
ዛሬ ሰለ ጫልቱ ሄለን መሆን በተጻፈው ላይ ትንሽ እላለሁ። ጫልቱ በለጠች ማለት ነው ጫላም በለጠ። ለኢትዮጵያዊ ጫልቱ ወይም በለጠች ከሄለን የበለጠ ትርጉምና ቅርበት ያለው ስም ነው። በጣም ደስ ያለኝ አቤ ቶኪቻው ተመሳሳይ ነገር ማንሳቱና የአዱገነት ልጆች ይህንን ጉዳይ የሚመለከቱት ለየት ባለ መነጽር መሆኑን ማሳየት መቻሉ ነው።
የቢሾፍቱው ልጅ ተስፋዬ በልጅነቱ አዲስአበባን ሁለቴ ብቻ ስላያት ያልተረዳው ነገር መኖሩን መግለጽና እግረመንገዱንም ያዘኑብን ይቅር እንዲሉን በሸገር ልጆች ስም ያለውክልና ለመጻፍ በመሻቴ ነው።  አዲስ አበባ ውስጥ የትኛውም አካባቢ የኖረ ሰው ሶስት አመት ሙሉ ኦሮምኛ ሲነገር አልሰማሁም ቢል በጣም ያስቃል። አዲስ አበባንም ያለማወቅ ይመስላል። እንኳን ኦሮምኛ ችሎ ለመጣ አዲስ አበባም ኖሮ ኦሮምኛ ማቀላጠፍ ይቻላል። ብዙዎቻችን ለዚህ ምሳሌ ልንሆን እንችላለን የኦሮሞ ልጆች መሆናችን አስፈርቶንም አሳፍሮንም አያውቅም። ተረብና ቀልድ ደግሞ ለሁሉም ዘር የሚሰጥ በመሆኑ በተለየ መልኩ ኦሮሞን ብቻ አንገት የሚያስደፋ አይደለም። ስለ ሌላ አገር የተጻፈ እስኪመስለን ድረስ የተቀባባ ነገር ነው። እንኳን ሀዘን ኖሮ በኦሮምኛ ማልቀስ ይቅርና የመስቀልን በዐል ውብ የሚያደርገውስ የማን ዘፈን ነበርና? ኦሮምኛ ሳይሞከርስ ከገጠር የመጣ ሸቀጥ እንዴት ይገዛ ነበር? በራሱ ዝቅተኛ ስሜት ውስጥ የገባና ራሱን መደበቅ የሚፈልግ ካልሆነ በቀር ኦሮምኛ መናገር የተከለከለባት ከተማ እስክትመስል ድረስ አዲስ አበባን ማጠልሸት በጣም አሳዛኝ ነገር ነው ውሸትም ነው። አማርኛ የስራ ቋንቋ በመሆኑ ብዙዎች ቋንቋውን እስኪማሩ ይቸገራሉ ይህ እውነት ነው። ሁዋላ ቀርነት በመኖሩ ቋንቋ ያለመቻልን መቀለጃ የሚያደርጉ ነበሩ ይህ ደግሞ ሁሉንም ይመለከታል። ኦሮምኛውን ስናወላግደው ዘመዶቻችን ይስቁብን ነበር። አንዳንዴም የአማርኛውን ቃል እንደ ኦሮምኛ ስናደርገው “ይሄ ደግሞ የሚበላ ነው የሚጠጣ” እያሉ የሚስቁብንን ጭምር አስታውሳለሁ።
አቴቴ የተከለከለ ነገር ሆኖ ሳይሆን ክርስትናን ከመቀበል ጋር የቀረ ነገር ነው። የግንቦት ልደታ አድባርም እንደዚሁ። ይህ ‘ዘመናዊነት’ በሚል ፈሊጥ የራስን የማጣጣል አባዜ እንጂ ሲስተሚክ ቫዮለንስም አይደለም። የተደራጁ ሃይማኖቶች የብዙዎችን አምልኮ አረመኔ የሚል ቅጥል እየለጠፉለት መስፋፋትን አድርገዋል። ይህ በመላው ዐለም የሆነ ነው። ይህ ማለት ምንም ጎጂ ነገር ማለትም ማንጓጠጥና መተረብ አልነበረም ለማለት አይደለም። የነበረ ነገር ነው በጣምም ስህተት ነው። ቋንቋችን ሀብታችን ነው ታሪካችን ነው ልንጠቀምበት ይገባል። አንድ ሁላችንንም ሊያገናኘን የሚችል ቋንቋ መኖሩ ደግሞ እንደ ሀገር አብረን እንድንኖርበት ያመቻቻል። አንዱ አንደኛው ላይ ሲሰለጥንበትና ሲጎዳው ይሁን ማለት ተገቢ አይደለም።
በጫልቱ ላይ የደረሰው ነገር ከልብ የሚያሳዝን ነው የዚህ አይነት ስነልቦና እንዲኖራቸው ለተገደዱት ሁሉ ልናዝን ተገቢ ነው። ሆኖ ያለፈን ነገር ፈጽሞ እንዳልነበር መካድም አይቻልም። ቢሆንም ይህ ድርጊት አንድን ዘር ለማዋረድ ሆን ብሎ የተነጣጠረ ክፋት እንዳልሆነ መረዳት ተገቢ ነው። አንዳንድ ጊዜም ለመብት መቆም ያለመቻልና ካለው ሁኔታ ጋር ተስማምቶ ለመኖር የሚደረግ ስህተትም ነው። ልክ እንደ ጫልቱ  ማንጠግቦሽ፣ ኩሪባቸውና አቻምየለሽ ከስማቸው ጋር በተያያዘ ብዙ ይተረቡ ነበር። አዝብጤና እርገጤን ሙደስርና ሙሽሪንም የማራቸው አልነበረም ከተሜ ያልሆነው ሁሉ ቅጽል ስም አያጣም ነበር። ከሸገር ልጆች ተረብ ያመለጡ ነብሶች ካሉ የታደሉ ናቸው። ከጎጃምም ይምጣ ከደሴ አዲስ ላይ ቅጽል ስም አይታጣለትም። ትክክል ነው ማለት አይደለም ግን ፈጽሞ በአንድ ዘር ላይ የተነጣጠረ ልዩ ጥቃት አይደለም። የሰውን ስሜት በዚህ ደረጃ ሊጎዳ የሚችል ቅጽል ስምም ሆነ ተረብ ጎጂ ከሆነ መስቀሉን መሸከም ያለባቸው አማርኛ የሚናገሩ የአዲስ አበባው ድብልቅ ኢትዮጵያውያን እንጂ አንድ ዘር የጥቃት ዒላማ ሊሆን አይገባም። አማርኛ ስለተናገሩ ብቻ አማራውን ሀጢአት ማሸከም ተገቢም ትክክልም አይደለም። ስህተትን በጥፋት ማረምም አይቻልም።
የኦርቶዶክስ ሃይማኖትና አማራን ማጥፋት ኢትዮጵያን የማፍረሻ ቁልፍ ነው ያሉትን የፋሺስት ጣልያኖች መርህ ለሚያስፈጽሙ ደግሞ፣ እንኳን የሰደበ የገደለም ይቅር የሚባባልበትን ባህል ያዳበረ ሕዝብ እንዳለን ልናስታውሳቸው ይገባል። የፋሺስቶቹን መርህ አራማጆቹንም ወገን ብለን አቅፈን ይዘን ብዙ ተጉዘናል። ለኛ ሞት ለመደገስ አይኑን የማያሸውን ተስፋዬንም እንደዚሁ። ያኔ ተቀለደባቸው ተሰደቡ ነው አሁን በኦሮሞ ልጆች ላይ የሚደርሰው ግፍ ምን ስያሜ ይሰጠዋል? ዘረኞች የራሳቸውን ጎሳ ብቻ ሽቅብ ሰቅለው በሌሎች ላይ ሊያደርሱ የሚችሉትን በደል የተመለከትነው አሁን ነው። ምናልባት ተስፋዬ ወደ ወለጋ አላቀና ይሆናል እንጂ እዚያ ደግሞ ጉራጌና አማራው ላይ ብዙ የሚያስቁ ቅጽል ስሞች ይሰጥ እንደነበር አስታውሳለሁ። ከዚያም ያለፉ ነገሮች ሆነዋል ግን ተማርን የሚሉ ጥቂት ሰዎች ያደረጉትን  የኦሮሞ ሕዝብ በሌላው ላይ እንዳለው ጥላቻ አድርጎ መውሰድ አላዋቂነት ነው። የኢትዮጵያ ገበሬ የመሸበትን አሳድሮ የራበውን አብልቶ የሚሸኝ ደግ ሕዝብ ነውና የጥቂቶቹን ክፋት ለሕዝቡ ማሸከም አይቻልም።
አዲስ አበባ ያለው አማርኛ ከዚህም ከዚያም ቃላት ተውሶ ኢተዮጵያንኛ ሆኖአል። እኔ ባደኩበት አካባቢ ስድስትም እንሁን ደርዘን ሁላችንም አንድ ዘር ሆነን አናውቅም። ድብልቅልቅ ነን። እናትና አባትም ከተለያየ ብሄረሰብ የተውጣጡ ሊሆኑ ይችላሉ። ይህ ለኛ ምንም ዋጋ አልነበረውም። ዘር ለመጥላት የሚያነሳሳ ምክንያትም እውቀትም አልነበረንም። ጥርት ያልኩ አማራ የሚለውም የአዲስ አበባ አማርኛ ሲቸግረው እናያለን።  ትልቁ ጥያቄ ይህ ሰዎችን እንደሚያሳዝን በመረዳት አሁን እንዳይደገም ማድረግና ከአንደበታችን የሚወጣውን መመዘን መቻልን ተምረናል ወይስ እዚያው ነን? የሚለው ነው። ባህላችን ሊያድግ ይገባዋል። መፍትሄው ወዲያና ወዲህ መሰነጣጠቃችን አይደለም መጥፎ ወይም ጎጂ የምንለውን ልማድ ማረም ማስተካከልና ከህግም አንፃር ተጎጂዎችን መታደግ የሚቻልበትን መንገድ በጋራ መፈለግ ይመስለኛል። ተስፋዬም ወደ መዝጊያው ላይ ወደዚያው የሚያንደረድር አረፍተነገር ማከሉ ከቡርቃ ዝምታ ጭፍን ጥላቻ ለመውጣት መሞከሩ ይመስለኛል። በዚህኛው ቅጹ ላይ ከአማራ ጥላቻ ወደ ሲስተሚክ ቫዮለንስ ዝቅ ብሎልናል ይህም የኦሮሞ ነጻ አውጪዎች የመገንጠል ጥያቄን ተወት ከማድረጋቸው ጋር ሊቀራረብበት የፈለገበት የብልጥ መንገድ ይመስለኛል። ተስፋዬ ስለ ኢትዮጵያ ግድ የሚለው ቢሆን ኖሮ ሌሎችንም በማማከር የአዲስ አበባው ባህል ምን ይመስል ነበር? ብሎ ትንሽ ምርምር ሊያደርግ በተገባው ነበር። አዲስ አበባ ተወልዶ ላደገ ኦሮምኛ በከተማው ብርቅ ነበር ቢለን ምናልባት መስማት የተሳነው ሰው ወይም በኦሮሞው ስም የፖለቲካ ትርፍ ፈላጊ መሆን አለበት እንላለን።
አዲስ አበባችን ከየትም መጣ ከየት ሰው ጦሙን የማያድርባት ከተማ ነበረች። የኢትዮጵያ ብሄር በሄረሰብ ጭማቂና ራሱን ዘመናዊ አድርጎ የሚጠራ ድብልቅልቁ የወጣ ሕዝብ የሚኖርባት ከተማ ናት። በስልጣኔና ዘመናዊነት ስም ዝርጠጣ፣ ተረብ፣ ስድብና ድብድብም እንደዚያው ጎላ ብሎ የሚታይባት ከተማ ነበረች። ንቅሳታሟን ኒቂሴ ብሎ የሚጠሩት ኦሮሞ ስለሆነች አይደለም መተረብ ስላለባቸው ነው። በዚህ አጠራር የኦሮሞ እናትና አባት ያላቸው ቋንቋውንም አሳምረው የሚናገሩ ልጆች ዘመዶቻቸውን ይተርባሉ። ከወሎም ትምጣ ከጎጃም ‘ኒቂሴ’ የሚለው ስም ሊለጠፍላት ይችላል። ትክክል ነው ማለት አይደለም። ፈጽም ‘ቡሊ’ ማድረግን አጥብቄ የምቃወም ነበርኩ። በልጅነት እድሜዬ በዚህ ምክንያት ቅር የሚሰኙ መኖራቸውን አሳምሬ አውቃለሁ። አንዳንዶችም ከተረብ ለመዳን የመጡበትን ጎሳ ይደብቁ እንደነበር አውቃለሁ። በመጡበት ጎሳ ምክንያት ትምህርት መማር ያልቻሉ ወይም የስራ እድል የተነፈጋቸው ካሉ በኔ እድሜ የማውቀው ባለመኖሩ መመስከር አይቻለኝም። በኦሮምኛ  ቅላጼ ብቻ የሚሳቅ የሚመስላቸው ሰዎች በጣም ተሳስተዋል። ኦሮሞው ግዕዝን ራብዕ ሲያደርጋት ወሎዬውም ‘ደ’ን ሲያጠብቃት ተረብ አለ። በወሎ ቅላጼ የአዲስ አበባ ልጆች በጣም ያፌዙ ነበር፣ በጎጃሙም በጎንደሩም እንደዚሁ። በትግሪኛውም ባልተለየ መልኩ ይቀለድ ነበር። ጉራጌስ ቢሆን ምኑ ተርፎ። ግን ይህ ሁሉየከተሜው ጉራ እንጂ  የዘር ጥላቻ አልነበረም። ይህን ሁሉ ጠልቶስ ማን መሆን ይቻላል? አሁንም ብዙ የአደባባይ ቀልዶች የዚህ አይነት አኪያሄድ አላቸው በሰላም ጊዜ ሊያስቅ ቢችልም በቀውጢ ሰዐት ግን መታረጃም ሊሆን እንደሚችል ሰዎች ልብ ሊሉት ይገባል። ከዚህ አይነት ቀልድ መታቀብም አለባቸው።
አዲስ አበባ ዘር የለም ‘ወልመካ’ ነው ድብልቅልቁ የወጣ። ለዚህም ነው ብዙ የአዲስ ልጆች ዘርህ ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠት የማይችሉት።  አዲሰ አበባ ጥቁር መሆን ያስተርባል፣ ቀይ መሆን ያው ነው። ትልቅ አይን ያለው ጉጉት ትንሽ ዐይን ያለው ጭልፊት ሊባል ይችላል። ቀጭኑ ሲምቢሮ ወይም ወፍ ሲባል ወፍራሙ ወደል ወይም ‘ቦዬ’። ረዥሙም ቀውላላ ነው አጭሩም ኩሩሩ። አፍንጫ ሲተልቅም ስም አለው ልጥፍ ሲሆንም እንደዚያው። እንደጊዜው መለዋወጥ ስም የመለዋወጡ ነገርም ያለ ነው። ይህ የሁላችንንም ስነልቦና የሚነካ ነው። አሁን ኦሮሞም አማራም ወደ መጽሀፍ ቅዱስና ቅዱስ ቁርዐን በመዝለቅ የአይሁድና የአረብ ስም መስጠቱን በሰፊው መያዙም የዚሁ ምሳሌ ነው። ኢዮብ የሚባል ደግና ትዕግስተኛ የመኖሩን ያህል ኢዮብ የሚባል ቀማኛ ሊኖር ይችላል። ስለዚህ አንድ ምሳሌ ሊገልጸው አይችልም። ተስፋዬ ሲባል ግን ወላጆች ራቅ አድርገው የሚመኙትን ይገልጻል። የተስፋዬ ወላጆች የተመኙትን በልጃቸው እያዩ ከሆነ ምንኛ ደስ ይላቸዋል። አርቲስቶቻችን ወደፈረንጅ ጠጋ የሚል በሁለት ፊደል የሚገለጥ ስም ፍለጋ ሲባዝኑ የምናስተውለውም ከዚህ ከጊዜ ጋር የሚመጣ ጉዳይ ነው። ማንጠግቦሽን ማኒ፣ ጎሳዬን ጆሲ ቴወድሮስን ቴዲ አይነት እንደማለት ነው። ይህ ግን ሲስተሚክ ቫዮለንስ ተብሎ ሊፈረጅ የሚችል አይመስለኝም።
ቀደም ባለው ጊዜ አንዳንድ ደካማ መምህራን ተማሪዎቻቸውን የሚያሳቅቁ ነገሮችን አላደረጉም ማለት አይቻልም። በርካታ የኦሮሞ ልጆች በዚህ አይነት ተረብና አስተማሪዎች አማርኛ ለመናገር ሲሞክሩ በሰደቧቸው ምክንያት አቂመው ከፍ ሲሉ ወደ ትግሉ እንደተቀላቀሉ ሲናገሩ ይደመጣል።  ይህ አገር ለመገንጠል ምክንያት ባይሆንም የፖለቲካ ትርፍ ተዝቆበታል። ይህ ባሁኑ ትውልድ እንዳይኖር ማስተማር አስፈላጊ ነው። እንደ ተስፋዬ ግምት ወይም ታሪኩን እነዳጫወቱት ሰዎች ግምት ከተማ ውስጥ የሆነው አማራ ኦሮሞ ላይ ያደረሰው በደል ሳይሆን ከተሜው በጅምላው ገጠሬው ላይ የነበረው ግብዝነት እንደሆነ መረዳቱ አስፈላጊ ነው። በደል አልነበረም፣ አልተደረገም ወይም ሆኖ አያውቅም የሚል የሚኖር አይመስለኝም። ማንም ቢሆን ተፈጥሮ በሰጠው መልኩ፣ ቤተሰብ በሰጠው ስሙና፣ አዲስ ቦታ ላይ አላዋቂ ሆኖ በመታየቱ ሊሰደብ አይገባም ብሎ መነሳቱ የተሻለ ነው። ከዚህ የፖለቲካ ትርፍ መፈለግ ግን ደካማነት ነው።የሆነው ሆኖ አልፏል በዚህ አይነት ሰው የማንኳሰስ ተረብ ምክንያተ ያዘኑ ወገኖች ለደረሰባቸው የስሜት መጎዳት በግሌ በጣም አዝናለሁ። እንደ ከተማው ልጅነቴም ይቅርታ እጠይቃለሁ የሸገር ልጆችም ይህንን ሰሜት እንደሚጋሩኝ አምናለሁ። እንደ አንዳንድ የጭቃ ወስጥ እሾሆች ደባ ግን የዘር ጥላቻ እንዳልሆነ አጥብቄ እሞግታለሁ።
ዘመናዊ ትምህርት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን መሸርሸሩን ልብ ያለማለት የራሳችንን ጥፋት ለመሸፈንም ምክንያት ሊሆን ይችላል። ምሁራን ባህላችንን ባህላዊ እውቀታችንን እንደ ሁዋላ ቀር በመቁጠር የፈረንጆቹን በመኮረጅ የነበረንን ሁሉ ሲኮንኑ መኖራቸውን ልንክድ አይገባም። በዚህ ምክንያት የኦሮሞውም ሆነ የአማራው ባህላዊ እሴቶች ወደ ጎን ተገፍተው ነበር። በዚህ ውስጥ ከኦሮሞው የወጡ ምሁራንም አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ሊቀበሉ ይገባል። ፈቅደን የተውነውን ተነጥቀን ነበር ብንልም ወደ እውነት የሚያመጣን አይመስለኝም። የሚበጀን ጣት መጠነቋቆልና ወንጀል መፈለጉ ሳይሆን ከዘመናዊ ኑሮ ጋር አጣጥመን ልናሳድጋቸው የሚገቡንን ባህሎቸ መመርመርና ጠቃሚ በሚሆን መልኩ መልሶ ማሳደጉ ተገቢም አስፈላጊም ነው። ተስፋዬም ሲስተሚክ ቫዮለንስን ሲተነትንልን ሀሳቡ ይገባን ይሆናል። እስከዚያው ግን ተስፍሽ ስለ አባት አገሩ እድገትና ብልፅግና ቢጨነቅና የኛን ለኛ ቢተውልን ይሻለዋል እላለሁ።

No comments:

Post a Comment