Friday, October 25, 2013

የጎሳ ፌዴራሊዝም

የአማራው ጎሳ የጅምላ መፈናቀልና አማራውን ለማጥፋት የሚደረገው ስልታዊ የወያኔ ትግሬዎች ዘመቻ

article 39


ክፍል አንድ
የወያኔ ትግሬዎችና ስለ አማራ ህዝብ ያላቸው ግንዛቤና የቆየ ጥላቻ ምን ይመስላል?
የወያኔ ሃርነት ትግራይ መሪዎችም ሆኑ ተከታዮቻቸው የትጥቅ ትግላቸውን ሲጀምሩ ለትግራይ ህዝብ ችግርና ኋላ ቀርነት ተጠያቂዎቹ ከዳግማዊ ዐጼ ምንሊክ ጀምሮ እስከ ደርግ መውደቅ ድረስ በስልጣን ላይ የነበሩት ወያኔ አማራ ብሎ የሚጠራቸው መንግስታት እንደ ነበሩ በፖለቲካ ፕሮግራም ደረጃ ቀርጸው የትግራይን ህዝብ እንዳስተማሩ ቀድሞ የወያኔ ድርጅት አባል የነበረውና ዛሬ በስደት በሚኖርበት አስውስትራሊያ ሆኖ የወያኔን እኩይ ዓላማ በቆራጥነትና በሃቅ እያጋለጠ ያለው አቶ ገብረ መድህን ዓርዓያ በቅርቡ “እነማን ነበሩ” በሚል ርእስ በመረጃ አስደግፎ አሳውቆናአል። የወያኔ ድርጅት የአማራው ህዝብ በእነዚህ የአማራ መንግስታት ብሎ በሚጠራቸው ከዐጼ ምንሊክ እስከ ደርግ መውደቅ ድረስ በነበሩት መንግስታት ዋነኛ ተጠቃሚ እንደነበረና የእነዚህም መንግስታት የስልጣን መሰረት እንደ ነበረ ሲያስተምር ቆይቶአል፤ ዛሬም ይህንኑ እያደረገ ነው ያለው። በዚህ ዓይነት የአማራን ህዝብ የእነዚህ ያለፉት መንግስታት የስልጣን መሰረት ነው በማለት ወያኔ የአማራውን ህዝብ ሲፈርጅ ቆይቶአል። የወያኔ ትግሬ መሪዎች የትግራይ ህዝብ ዐጼ ምንሊክን በመሳሰሉት የአማራ ተወላጆች የሆኑ የኢትዮጵያ መሪዎች እንደ ኢትዮጵያዊ እንደማይታይ ለትግራይ ህዝብ ያስተምሩ ነበር። እነዚህም የትግራይን ህዝብ እንደ ኢትዮጵያዊ የማይቆጥሩ የአማራ መሪዎች የትግራይን ህዝብ ሆን ብለው እንዴት ለችግር፤ ለጎስቁልናና ለእንግልት እንዳበቁት የወያኔ ድርጅት መሪዎች (ዛሬ በስልጣን ላይ ያሉትም ሆኑ ድርጅቱን ጥለው በመውጣት ዛሬ ተቃዋሚ ነን ብለው የዛሬው የትግራይ ህዝብ ሰቆቃ ከደርግ ጊዜው የባሰ ነው ብለው የሚነግሩን ጭምር) በሰፊው አስተምረዋል። እንግዲህ የወያኔ መሪዎች የአማራ ንጉስ ብለው በሰየሟቸው በዐጼ ምንሊክ ተጀመረ ያሉት የትግሬዎች ጭቆና ተከታዮቻቸው ናቸው በሚሏቸው የዐጼ ሃይለ ስላሴና የደርግ መንግስታትም ዘመን ቀጥሎ የትግራይ ህዝብ በመጨረሻ ተማሮ “የአማራውን የደርግ” መንግስት ለመጣል እንደ ተነሳ እንረዳለን። የወያኔ መሪዎች የትግራይን ህዝብ ችግር የአማራ ተወላጆች በሚላቸው የኢትዮጵያ መሪዎች እንደተፈጠረ አድርገው እንዴት እንደሚያዩና እንደሚቀሰቅሱ ሩቅ ሳንሄድ እዚሁ እኔ በምኖርበት በሆላንድ ሀገር በስደት የሚኖረው የቀድሞው የወያኔ ድርጅት መሪና ጠቅላይ የጦር አዛዥ አረጋዊ በርሄ ወያኔን ተቃዋሚ ነኝ ብሎ ካለ በኋላ እንኩዋን በሚከተለው መልክ ከጻፈው ጽሁፍ እንረዳለን።
menelik
እምዬ ምንሊክ
የሸዋው የፊውዳል ባላባት የሃይለ መለኮት ልጅ (ምንሊክእንደማናቸውም የሸዋ መኳንንቶች ሁሉ ከጥንት ጀምሮ በጣም የስልጣንጥመኛና ፀረ-ትግሬ የነበረ ሰው ነበረ። በንግስ ዘመኑ ሁሉ ዳግማዊምንሊክ የዘመናዊ የጎሳ ቅራኔና ግጭት ዋና ፈጣሪ ነበር። ዳግማዊምንሊክ በአድዋ በጣሊያን ላይ የተጎናፀፈውን ድል ተቀናቃኞቹ ሊሆኑበሚችሉት በተለይም በመንገሻ ዮሃንስና በአሉላ አባ ነጋ አመራር ሥርበነበሩት የትግራይ መኩዋንንቶች ላይ ከፍተኛ የበላይነትን እንዲቀዳጅአደረገው። ዳግማዊ ምንሊክ ትግራይን የመከፋፈልና የማዳካም ዕድልነበረው። የምንሊክ ጦር የጣሊያኑ የቅኝ ገዢዎች ጦር ያደረሰውን ያህልጥፋት እንዲያደርስ በትግራይ ላይ መረን ተለቀቀ። የትግራይ ህዝብይህንን ጊዜ ዘመነ ሸዋ ብሎ ያስታወሰዋል፤ ይህም ማለት ትግራይበሸዋ አገዛዝ ሥር  የወደቀብት ዘመን ማለት ነው። የምንሊክ አቋምየተመሰረተው በሥልጣን ወዳጅነቱና ትግራይ ሊናቅ የማይገባው ጠላትነው በሚለው አመለካከቱ ላይ ነበር። በርካታ የትግራይ ምሁራንምንሊክ ትግራይን እንደራሱ ህዝብ የማያይ አድርገው ይቆጥሩታል።የምንሊክ ሰሜኑን የመከፋፈልና የማዳከም ሃሳብ የትግራይን ግማሽጣሊያን በቅኝ ግዛትነት ይገዛው ዘንድ በመስጠት ሂደት የታጀበ ነበር።ምንሊክ አፍሪካ ለቅርጫ በቀረበችበት ዘመን ጣሊያን ኢትዮጵያን ቅኝየማድረግ ፍላጎት እንደነበራት እምብዛም እውቀት አልነበረውም።ምንሊክ ትግራይ አንዴ ለሁለት ከተከፈለች እሷን እንደፈለጉ መግዛትይቻላል ብሎ ያምን ነበር። ትግራይን ለመቅጣት ምንሊክ በየዋህነትየወቅቱ የቅኝ ገዢዎች ወጥመድ ውስጥ ገባ። ኢጣሊያ የምንሊክንድክመት በመጠቀም ወደ ደቡብ (ማለትም ከኤርትራ ወደ ትግራይመስፋፋት ቀጠለች። ምንሊክ ጣሊያኖች ኤርትራን ይዘውእንዲቆዩ ያደረገበትን ምክንያት በተመለከተ ክርክር ውስጥ ሳንገባ አንድ የማይካደው ሃቅ ግን ትግርኛ ተናጋሪው ህዝብ ለሁለት ጌቶችማለትም ከመረብ በላይ ያለው ህዝብ ለጣሊያን፤ ከመረብ በታች ያለው ህዝብ ደግሞ ለምንሊክ ተከፍሎ ተሰጠ። ይህ ለወትሮውአንድ ወጥ በነበሩትና አንድ ላይ ቢሆኑ (የምንሊክንሥልጣን ለመቀናቀን በሚችሉት ትግሬዎች መካከል የተፈጠረው ከፋፋይመስመር (fault line) መነሻ ወይም ምንጭ ነው። በዚህም ምክንያት ነው የሸዋ አማራ የገዢ መደብ ትግሬዎችን የማዳከም ዘመቻበዚህ ታሪካዊ ወቅት የተጀመረው:: (Aregawi Berhe,  ”Origins & Development of the National Movement in Tigrai; a Socio-historical Analysis”,  Institute of Social Studies, the Hague, 1993 (Aregawi Berhe was former chairman of the TPLF አረጋዊ በርሄ እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ ዓ.ም ሆላንድ ውስጥ ሄግ ከተማ በሚገኘው ኢንስቲትዩት ኦፍ ሶሻል ስተዲስ በተሰኘው ተቋም ውስጥ ለማስተርስ ዲግሪው በእንግሊዘኛ ቋንቋ ከጻፈው የተወሰደ (ጥቅሱን ከእንግሊዘኛው ወደ አማርኛ የተረጎምኩት እኔው እራሴ ነኝ)።
ከላይ ከጠቀስኩት የአረጋዊ  ጽሁፍ እንደምንረዳው አረጋዊና ተከታዮቹ ታሪክን በመከለስ ኢትዮጵያን ከጣሊያን የቅኝ አገዛዝ እንዲከላከልና ነጻነቷን እንዲያስጠብቅ የተደረገለትን ጥሪ ተቀብሎ በዐጼ ምንሊክ መሪነት የዘመተውን ከመላው የኢትዮጵያ ክፍሎች የተውጣጣ የኢትዮጵያ አርበኛ ትግራይን ወሮ ዘረፈ፤ አደኸየ ብለው ወነጀሉ። በዚህም ምክንያት የአድዋ ዘመቻ አዝማችና መሪ የነበሩት ምንሊክንና  የአማራ ህዝብ በትግራይ  ልሂቃን ዘንድ እንደ ጠላት ተቆጥረው ከትውልድ ትውልድ የተላለፈ የትግሬዎች ጥላቻ ዒላማ ሆኑ። እስቲ ከዚህ በታች የወያኔ ድርጅት የፖለቲካ ፕሮግራም ስለ አድዋ ጦርነትና እሱን ተከትሎ መጣ ስለሚለው የትግራይ መጨቆን ያለውንእንመልከት።
1881 ..  ትግራይ እንደገና በሸዋ አማራ ገዢዎች አፈናና ጭቆና ስር ወደቀች። ከባድ ታክስ በትግራይ ህዝብ ላይ ተጣለ።በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሆን ተብሎ ካለ ስንቅ የተላኩ የምንሊክ ጦር ወታደሮች የትግራይን መንደሮች ዘረፉት። ባጭር ጊዜ ውስጥየትግራይ ህዝብ የኢኮኖሚና የማሀበራዊ ሁኔታ በፍጥነት አሽቆለቆለ። ከዚህ በተጨማሪ ሆን ብሎ የትግራይን ህዝብ ቋንቋ ባህልናታሪክ ለመጫን እርምጃዎች ተወሰዱ። እነዚህ የጭቆና እርምጃዎች የትግሬዎችን ብሄረተኛ ስሜት በመቀስቀስ ኃይለኛ የሆነ ብሄራዊቅራኔን ፈጠሩ TPLF Political Program adopted at the Second Congress,1983 (ለዝርዝሩ በሁለተኛው  የወያኔ ሀርነት ድርጅት ጉባኤ ላይ የጸደቀውን የ1975 ዓ.ም. የፖለቲካ ፕሮግራም ይመልከቱ) (ከላይ የጠቀስኩትን ከእንግሊዘኛው ወደ አማርኛ የተረጎምኩት እኔው እራሴ ነኝ)።
የትግራይ ብሄረተኞች እየሰሙ ያደጉትን ሀሰተኛ የምድጃ ዳር ታሪክ በተመለከተ የሚከተለውን ለአንባቢ ላስተዋውቅ፤
በዚያ ቀን የሸዋ ሰራዊት መቀሌን ሙሉ በሙሉ ዘረፈው፤ በአካባቢው የነበሩ መንደሮችም በሙሉ ተዘረፉ። እንደርታምእንዳልነበረች ሆነች። በየመንገዱ ትልቅ ትንሽ ህፃን ሳይሉ ሰለቡት። ቀጥሎም የምንሊክ ሰራዊት እንደርታን አወደማት። እንዳልነበረችሆነች። ብቻ የወንድ ልጅ ይሁን እንጂ የተገኘ ሰው ሁሉ ይገደላል። የእንደርታ ሰዎችም ቢሆኑ ዝም ብለው አልታረዱም። በየቋጥኙናበየጫካው እየተደበቁ የምንሊክን ሰራዊት ሲፋለሙት ነበር። የምንሊክ ሰራዊት የመግደልና የመስለብ ሱስ ያለበት ነው። ሰዎችንበገደለና በሰለበ ቁጥር ይፎክራል። ሌላው ይቅርና በመላ ኢትዮጵያ የተከበረውን የአብርሃ ወአጽብሃ ገዳምም እንዳለ ዘርፈውታል(ምንጭ፤ ገብረ ኪዳን ደስታ የትግራይ ህዝብና የትምክህተኞች ሴራ ከትላንት እስከ ዛሬ በሚለው መጽሃፉ ውስጥ ከጠቀሰው ታሪክኢትዮጵያ በሚል ርዕስ በትግርኛ ቋንቋ ከታተመው መጽሃፍ የተጠቀሰ።
ስለ አማራ ህዝብና ስለ እነ ዐጼ ምንሊክ፤ ዐጼ ሃይለስላሴ ወዘተ በወላጆቻቸው ጥላቻን እየተጋቱ ያደጉት የዛሬዎቹ የወያኔ መንግስት መሪዎች ከልጅነት ጀምሮ ጥርሳቸውን ሰብረው ያደጉበትን በምድጃ ዳር የተማሩትን የጥላቻና የውሸት ታሪክ ከዘመናዊ የብሄረተኛነት አስተሳሰብ ጋር አዳቅለው አክራሪውንና ዛሬ ኢትዮጵያን እያፈረሰ ያለውን የትግራይ ብሄረተኛነት በማቀንቀን ኮትኩተው አሳደጉ። ዛሬ የትግራይ ብሄረተኛነት ጥቂቶች የሚጋሩት እብደት ሳይሆን እንደ ጀርመኑ የናዚ ወይም Aregawi-berhe-እንደ ጣልያኑ የፋሽዝም ርዕዮተ ዓለም በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ የጎሳ ተወላጆቹን አስተሳሰብ በመቀየርና ከሰውነት ደረጃ በማውጣት የወያኔ ትግሬዎች ከትግሬ ጎሳ ውጭ ያለውን ኢትዮጵያዊ በተለይ ደግሞ የታሪክ ደመኛችን ነው የሚሉትን የአማራን ህዝብ እንደ አደገኛ አውሬ የሚያዩበትና የዚህንም ህዝብ ህልውና ጨርሰው ለማጥፋት የተነሱበት ደረጃ ላይ አድርሶአቸዋል። የትግሬዎች አካላዊ ገጽታ፤ መልክ፤ ባህልና ታሪክ ከሌላው ኢትዮጵያዊ ጋር መመሳሰል ሌላው ኢትዮጵያዊ የወያኔ ትግሬዎችን እንደ እራሱ ወገን እንጂ ለኢትዮጵያና ትግርኛ ተናጋሪ ላልሆኑ ኢትዮጵያውያን ይህን ያህል ጥላቻ ያላቸው ወገኞች ናቸው ብሎ እንዳይገምት አድርጎታል፤ አዘናግቶታልም። ስለዚህም የኢትጵዮጵያ ህዝብ የወያኔ ትግሬዎችን እዚህ ደረጃ ላይ ሳይደርሱና ብዙ ጥፋት ሳያደርሱ ሊያቆማቸው የሚችልበት ብዙ አጋጣሚዎች አልፈውታል። ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ በሀገራችን በህዝቡ ዘንድ ቀርቶ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ነን በሚሉት ዘንድ ስለ ጎሳ ብሄረተኛነት (ethnic nationalism) ያለው ግንዛቤ እጅግ የሚያሳዝን በመሆኑ ዛሬ ወያኔ እያደረሰ ያለውን የጎሳ ጽዳትና ጎሳን መሰረት የጅምላ ፍጅት ይከሰታል ብለው ለማሰብ አልቻሉም። በኢትዮጵያ ረጅም ታሪክ ውስጥ ያንድ የኢትዮጵያ ጎሳ አባሎች (ትግሬዎች) የመንግስት ስልጣን ይዘው አንተ ይኸ ክልልህ ስላልሆነ ከዚህ ለቀህ ውጣ በማለት የሌሎችን ጎሳ አባላት (አማራን፤ አፋርን፤ አኑዋኮችን ወዘተ) እንደ አውሬ በጦር መሳሪያ የሚያሳደዱበትን፤ ህጻናትና አሮጊቶች ሽማግሌዎችና አቅመ ደካማዎችን ለሞትና ለዘግናኝ ስቃይ የሚዳርጉበት ዘመን ታይቶ አይታወቅም።
የወያኔ ትግሬዎች ዓላማ አማራ ብለው የሰየሙትን ጨቋኝ የደርግ ስርዓት ጥለው ለትግራይ ህዝብ ህይወት የሚያሻሽል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ማምጣት ነበር። ይህንን ዓላማቸውን አስመልክቶ የቀድሞው የወያኔ መሪ በ ዓ.ም በጻፈው ጽሁፍ የሚከተለውን ብሎ ነበር። የትግራይ ህዝብ የወል ምኞት ጨቋኙን የአማራ (የደርግ) መንግስት መጣል ብቻ ሳይሆን የራሳቸውን (የትግሬዎችን) ህይወት የሚያሻሽል የማህበራዊና የኢኮኖሚ ለውጥን ማምጣት ነበር”። አረጋዊ በርሄ “How the Media of the TPLF Emerged and Countered the Dominant Media of the Ethiopian State: Can it be a Viable Alternative for Social Transformation?”, a paper written by Aregawi Berhe for a degree at the Hague Institute of Social Studies, 1992) (ጥቅሱን ከእንግሊዘኛ ወደ አማርኛ ትርጉም የራሴ የአሰፋ ነጋሽ ነው)። ይህን ከላይ አረጋዊ በርሄ የገለጸውን የወያኔ ዓላማ በማሳካት በኩል ባለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት የወያኔ ትግሬዎች መንግስት ምን እንዳደረገ፤ እንዴት የትግራይን ገጽታና የትግራይ ተወላጆችን ህይወት ጉልህና አዎንታዊ በሆነ መልክ እንደቀየረ ማንም የኢትዮጵያን ጉዳይ የሚከታተል፤ እንደዚሁም በራሱ ሀገር የበዪ ተመልካች የሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ ስለሚያውቀው ዝርዝር ውስጥ ለመግባት አልፈልግም። የትግራይ የጎሳ ብሄረተኞች ግን ባለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት ለህዝባቸው ያለሙትን ልማትና ማህበረሰባዊ ለውጥ እንዳመጡ መካድ አይቻልም።
የጎሳ ፌደራሊዝም፤ ማንነት ላይ የተመሰረተ ፖለቲካና የጎሳ ግጭት በኢትዮጵያ
የወያኔ መንግስት የተመሰረተበትና በዛሬይቱ ኢትዮጵያ የመንግስታዊ ስርዓት መሰረት የሆነው የጎሳ ፌደራሊዝም የጎሳን ማንነትና ልዩነትን ዓይነተኛ የፖለቲካ ማደራጃ አድርጎአቸዋል። የጎሳ ፌዴራሊዝም ዲሞክራሲያዊ ሳይሆን ኢ-ዲሞክራሲያዊ ነው። ዲሞክራሲ ሁሉን አሳታፊ እንጂ አንድን ግለሰብ በጎሳ ማንነቱ ምክንያት ከፖለቲካ ተሳትፎ ውጭ የሚያደርግ አይደለም። ፖለቲካ በጎሳ ማንነትና መስፈርት ላይ ተመስርቶ አንድን ሰው አንተ የእኔ ጎሳ አባል አይደለህም ብሎ በጎሳ ማንነቱ ምክንያት ሲያገል፤ ሌላውን ደግሞ አንተ የጎሳ አባሌ ነህ ብሎ ሲያሳትፍና ሲያቅፍ፤ ይህን አይነቱ ጎሳን መሰረት ያደረገ ፖለቲካ ዲሞክራሲ የሚባለውን አስተሳሰብ በጽኑ ይቃረናል። በዚህም ምክንያት በጎሳ ማንነት ላይ ተመስርቶ የሚደራጅ የፖለቲካ ስርዓት በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ ያሉ የተለያየ የእምነት ተከታዮች፤ የተለያዩ የጎሳ ተወላጆች እንደ ሰው ወይም እንደ ሰብዓዊ ፍጡር በሚያስተሳስሯቸውና በሚጋሯቸው በርካታ ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ እንደ አንድ ሀገር ዜጎች እንዳይገናኙ የሚያደርግ በመሆኑ አፍራሽ እንጂ ገንቢ አይደለም። የጎሳ ፌዴራሊዝም በአንድ ሀገር ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች በልዩነቶቻቸው ላይ እንዲያተኩሩ በማድረግ ሊያቋርጥ የማይችል ጥላቻን በማራገብ ለጋራ ጥፋትና እልቂት የሚጋብዝ፤ በባህል መጠበቅ፤ በጎሳ መብት መጠበቅ ስም ያንድ ጎሳ ልሂቃን እኛ የዚህ ጎሳ ብቸኛ ተወካዮች ነን ብለው ባንድ ነጻ ማህበረስብ ውስጥ ሊደረግ የሚገባውን በጎሳ ማንነት ሳይሆን በፖለቲካ አስተሳሰብ ላይ የተመሰረተ ጤናማ የፖለቲካ ውድድር ወይም ፉክክር የሚሸሹበትን ኢ-ዲሞክራሲያዊ አመለካከትና አሰራር ያራምዳል። ይህም የጎሳን ማንነት መሰረት ያደረገ የፖለቲካ ስርዓት ወደ ፋሽስታዊ የዘር ፍጅትና የእርስ በርስ ጥላቻ የሚያመራ አደገኛ ርዕዮተ ዓለም ነው። የፈረሰችው የትላንትናዋ ዩጎዝላቪያ የጎሳ ፌዴራሊዝም በአንድ ሀገር ላይ የሚያስከትለውን ጥፋትና ፍጅት አሳይታናለች። የጎሳ ፌዴሊዝም አንዱን ሕዝብ በሌላው ላይ ያነሳሳል ምክንያቱም የጎሳ ፌደራሊዝም ባፈጣጠሩ ህዝብን በሚለያይ ማንነት ላይ የተመሰረተና በልዩነት ላይ  ያተኮረ ስለሆነ ነው። የጎሳ ፌደራሊዝም የጎሳን ማንነት ብቻ በማጉላት ሌሎች የማንነት መገለጫዎችንያደበዝዛል፤ ያንድ ሃገር ዜጋዎች በመካካላቸው የግንብ አጥር እንዲሰሩ ያደርጋል፡ ያለያያል፡ ያቃቅራል። አንድ-ወጥ ጎሳ ለመፍጠርና “ንጹህ ደም ያላቸውን የአንድ ጎሳ ተወላጆች” ባንድ ኩታ-ገጠም ክልል ውስጥ ለማሰባሰብ የሚደረገው ጥረት በግድ ከዚያ ከንጹሁ ጎሳ ተወላጆች ውጭ ያሉትን የሌሎች ጎሳ  ተወላጆችን “ከንጹሁ ጎሳ ተወላጆች” ክልል በሃይል ወደ ማስወጣቱ የጭፍጨፋ ሂደት ያመራል። ትላንት በምስራቅ ወለጋ፤ በጉራ ፈርዳ ዛሬ ደግሞ በቢኒሻንጉል የታየው ዘግናኝ ድርጊት የጎሳ ፌዴራሊዝም ውጤት ነው። የጎሳ ፌዴራሊዝም ዋና አራማጅ
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ (ፎቶ: addis fortune)
የሆኑት የኦሮሞ ብሄረተኛ አቶ ቡልቻ ደመቅሳ አሜሪካን ሀገር ይታተም በነበረ ኢትዮጵያን ኤክዛምነር (Ethiopian Examiner) በሚባል መጽሄት እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በሰኔ ወር 1993 በጻፉት አንድ መጣጥፍ ውስጥ የሚከተለውን ሃሳብ አስፍረው ነበር።  “ኦሮሞዎች የኦሮሞ ዞኖች ወይም ቀጠናዎች ሁሉ ባንድ ላይ ተጠቃለው አንድ የኦሮሞ ክልል ሥር እንዲሆኑ ይፈልጋሉ (Bulcha Demeksa, Ethiopian Examiner, June 1993)። ይህ የአቶ ቡልቻ ሃሳብ በረጅም ትልሙ አንደ-ወጥ (ethnically homogenous) የሆነ ያንድ ጎሳ ተወላጆች ብቻ የሚኖሩበት ክልል ለመፍጠር፤ ብሎም ከኦሮሞ ጎሳ ውጭ ያሉ ሌሎች ጎሳዎችን በማስወገድ ራሱን የቻለ አንድ ነጻ ሀገር ለማቋቋም ያለመ ሂደት መሆኑን ማንም የማገናዘብ ችሉታ ያለው ሰው ይረዳል። ጎሳን መሰረት ያደረገ ክልል በመጨረሻ እናንተ የእኛ ጎሳ አባሎች ስላልሆናቸሁ ከዚህ ውጡ ወደሚለው የጎሳ ጽዳት ( ethnic cleansing ) እንደሚያመራ ትላንት በምስራቅ ወለጋ፤ በጉራ ፈርዳ፤ በቤኒሻንጉልና በኦጋዴን የተከሰተው ሁኔታ ያሳየናል። አቶ ቡልቻ ደመቅሳ የጎሳ ፌዴራሊዝም በኢትዮጵያ ተቀባይነት ያለውና ጭራሽ ሊቀለበስ የማይችል እውነታ መሆኑን በሚከተለው መንገድ እርግጠኛ ሆነው በዚሁ ኢትዮጵያን ኤክዛምነር በተሰኛው ባንድ ወቅት በአሜሪካ ይታተም በነበረው ወርሃዊ መጽሄት ላይ እ. አ. አቆጣጠር በግንቦት 1993 በጻፉት ጽሁፍ ውስጥ ይነግሩናል። “በኢትዮጵያ በጎሳ ላይ የተመሰረተው ፌዴራሊዝም ወደ ኋላ ሊመለስ አይችልም ምክንያቱም አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ ይፈልገዋልና”( Bulcha Demeksa, Ethiopian Examiner, May 1993) አቶ ቡልቻ ይህንን ከፍተኛ ድፍረት የተሞላበት፤ በጥናትና መረጃ ላይ ያልተመሰረተ አስተያያት ሲሰጡ ድፍን የኢትዮጵያ ህዝብ ቀርቶ እሳቸው በደንብ አውቀዋለሁ፤ ጥቅሙን አስጠብቅለታለሁ የሚሉትን የኦሮሞን ህዝብ እንኳን ጠይቀው፤ አስተያየቱንና ፍላጎቱን ሰብስበው አይደለም። በወያኔ ትግሬዎች መንግስት ከተደረገው ከአስራ አራት ዓመታት የጎሳ ፖለቲካ ሰበካ እንኳን በኋላ የኢትዮጵያ ህዝብ ለጎሳ ፌዴራሊዝም ልቡን እንዳልሰጠ በግንቦት ወር 1997 ዓ. ም የተደረገው ብሄራዊ ምርጫ አሳይቷል። በጎሳ ሳይሆን ሀገር-አቀፍ አጀንዳ አንግቦ ውድድር ውስጥ የገባው የቅንጅት ድርጅት ያገኘው ከፍተኛ ድጋፍ የአቶ ቡልቻንና ከወያኔ ጀምሮ እስከ ዛሬዎቹ የመድረክ አባሎች ድረስ ያሉትን የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች ክፉኛ አስደንግጦአል። መድረክም የዚህ የጎሳ ፖሊቲካ ክስረት ያስደነገጣቸው የጎሳ ፖለቲካ ድርጅቶች ስብስብ ሆኖ ብቅ ያለው ይህንን የጎሳን ፖለቲካ ውድቀት በጋራ ሆኖ ለመከላከል፤ ጎሳ-ዘለልና ሀገር-አቀፍ ኢትዮጵያዊ የፖለቲካ አጀንዳ ያላቸውን ወገኖች በኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ ያላቸውን ተቀባይነት ለመዋጋት ነው። የእነ ሰዬ አብርሃም ከወያኔ ወጥቶ መድረክ መግባት አልሸሹም ዞር አሉ ነው፤ ወደዚያው ጥርሱን ወደነቀለበት የጎሳ ፖለቲካ የደራበት የመድረክ ሰፈር ተመልሷል።  የዚህ ጽሁፍ ሁለተኛው ክፍል ከዚህ ቀጥሎ ይቀርባል!!!!!!
ክፍል ሁለት
የጎሳ ፌዴራሊዝምና የኢትዮጵያዊ ዜግነት መብት በኢትዮጵያ
በቅርቡ የአማራ ጎሳ ተወላጆችን መፈናቀል አስመልክቶ አስያየታቸውን ከሰጡ ግለሰቦች መካከል አፍቃሪ-ኦነግ የሆነው የኦሮሞ የጎሳ ብሄረተኛ ጃዋር መሀመድ ለአንድነት ጋዜጣ የአማራው ህዝብ ችግር ተቆቋሪ በመምሰል በሰጠው ቃለ መጠየቅ አማራው ከቤኒሻንጉል የተፈናቀለው በወያኔ ተንኮል እንጂ የጎሳ ፌዴራሊዝም ባመጣው ችግር ምክንያት አይደለም በማለት የጎሳ ፌዴራሊዝም ውጤት የሆነውን ችግር ለማስተባበል ሞክሮአል። ጃዋር የአማራው ህዝብ መፈናቀል ምክንያት የወያኔ መንግስት ተንኮል እንጂ የጎሳ ፌዴራሊዝም ፖሊሲ የፈጠረው ችግር አይደለም በማለት የጎሳ ፌዴራሊዝም የዜግነትን መብትና ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በፈለገበት ክልል ሂዶ የመኖርና ህይወቱን የመምራት መብት እንዳለው አድርጎ ለማቅረብ ሞክሮአል። ይህ እጅግ ስህተተኛና የጎሳ ፌዴራሊዝምን አጥፊነትና ሀገር-አፍራሽነት፤ የጎሳ ግጭትና የጥላቻ ፈጣሪነት ለመካድና ለመሸፋፈን የሚደረግ ጥረት ነው። እንደ ጀዋር መሃመድ ያሉ የነጻይቱን ኦሮሚያ ሀገር መፈጠር የሚጠባበቁ የኦሮሞ ብሄረተኞችም ሆኑ በሀገር ቤት ተደራጅተው በሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ (የአቶ ቡልቻ ደመቅሳና የዶክተር መረራ ጉዲና ድርጅቶች ተዋህደው የፈጠሩት የጎሳ ፌዴራሊዝም አራማጅ ድርጅት ነው) ድርጅቶች፡ እንደዚሁም ሌሎች የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች ይህ ዛሬ በወያኔ ትግሬዎች መንግስት ስራ ላይ የዋለው የጎሳ ፌዴራሊዝም ስርዓት በመጨረሻ ኢትዮጵያን በጎሳ ወደሚበታትንንና የሚመመኙትን ነጻ ኦሮሚያን፤ ኦጋዴንያን፤ ወዘተ ምስረታ ሂደት እያመራ መሆኑን ጠንቅቀው ያውቃሉ። በጎሣ ማንነት ላይ የተመሰረተው የጎሳ ፌዴራሊዝም ስርዓት የግለሰብን መብትና ነጻነት የዲሞክራሲያዊ ስርዓት መገለጫ አድርጎ ስለማያይ፤ እንዲያውም ይህንን የግለሰብ መብት ስለሚጻረርና ከግለሰብ መብት በፊት የቡድንን መብት ስለሚያስቀድም በተፈጥሮው ዴሞክራሲን ይጻረራል። ቬስና ፖፖቭስኪ የተባለች ጸሀፊ እንዳለችው “ዘመናዊ የዲሞክራሲ ጽንሰ ሃሳብ የተመሰረተው በጎሳ ወይም በብሄር-ብሄረሰብ ማንነት ላይ ሳይሆን በግለሰብ ነጻነትና ምርጫ ላይ ነው። አንድ ግለሰብ የፖለቲካ ነጻነቱን (የዜግነት መብቱን) የሚቀዳጀው በጎሳው አማካይነት ሳይሆን ራሱ ነጻ ሰው ሆኖ የሚፈልገውን መምረጥ ሲችል ብቻ ነው። በትክክለኛ መንፈሱ አንድ ግለሰብ የፖለቲካ ነጻነቱን የሚጎናጸፈው በጎሳው አማካይነት ሳይሆን ራስ-በቅ ዜጋ ሆኖ ነው” (Vesna Popovski, Yugoslavia: Politics, Federation, Nation, 1995) (ጥቅሱን ከእንግሊዘኛው ወደ አማርኛ የተረጎምኩት እኔው እራሴ ነኝ).
እስቲ የወያኔ ህገ መንግስት የሚደነግገውን ህገ መንግስታዊ ድንጋጌ ከዚህ ቀጥለን እንመልከት።
የወያኔ መንግስት የደነገገው ህገ መንግስት አካል የሆነው ጠንቀኛው አንቀጽ ፰ ፡
አንቀጽ ፰ የህዝብ ሉዓላዊነት ።
፩ – “ኢትዮጵያ ብሄሮች፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የኢትዮጵያ ሉዓላዊ ስልጣን ባለቤቶች ናቸው።
፪ – ይህ ህገ መንግስት የሉዓላዊነታቸው መገለጫ ነው።
፫ – ሉዓላዊነታቸውም የሚገለጸው በዚህ ህገ መንግስት መሰረት በሚመርጧቸው ተወካዮቻቸውና በቀጥታ በሚያደርጉት ዲሞክራሲያዊ ተሳትፎ አማካይነት ይሆናል”።
ይህ ከላይ የተጻፈው አንቀጽ ከውጭ ሲያዩት ለኢትዮጵያ ህዝብ መብት የሚያጎናጽፍ ቢመስልም፤ መብትና ስልጣን የሚያጎናጽፈው ወያኔብሄሮች፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ለሚላቸው ምንነታቸውና ልዩነታችው እንኳን በቅጡ ተለየተው ላልታወቁ ስብስቦች ነው። በዚህም ምክንያትይህ አንቀጽ በማንኛውም ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ውስጥ የሚታወቀውን የአንድን ሰው የዜግነት መብት በህገ መግንስቱ ውስጥ አይደነግግም። በዚህም ምክንያት ይህ ህገመንግስት መብት ከየሚሰጠው ብሄሮች፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ለሚባሉ በቋንቋ መስፈርት ለተለዩ ክልሎች ነው። በዚህ ህገ መንግስት መሰረት አንድ ግለሰብ መብቱ የሚታወቅለት የጎሳ ማንነትን መሰረት አድርገው በተሰየሙት ብሄር፤ ብሄረሰብና ህዝቦች በሚባሉት ስብስቦች በኩል ነው። አንድ ሰው መብት የሚኖረው የእነዚህ ብሄር፤ ብሄረሰብና ህዝቦች የሚባሉ ስብስቦች አባል በመሆን ነው እንጂ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ ዲሞክራሲያዊ ሀገሮች ውስጥ እንደሚታየው በግለሰብ ሰውነቱ እንደ አንድ የኢትዮጵያ ዜጋ አይደለም። ስለዚህ አንድ ኢትዮጵያዊ የሚኖረው መብት በጎሳ ማንነት ላይ ተመስርተው በታወቁት ብሄር፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች በሚባሉ ስብስቦች አማካይነት ብቻ ነው የሚረጋገጥለት።  አንድ ኢትዮጵያዊ መብቴ ነው ብሎ የሚለውም ነገር ተቀባይነት ያለው በእነዚህ በጎሳና በቋንቋ መስፈርት ተለይተው በታወቁት ክልሎች ውስጥ ነው እንጂ በመላው የኢትዮጵያ ክፍሎችና ክልሎች ውስጥ አይደለም። ስለዚህ ዛሬ ኢትዮጵያ በምትደዳደርበት ህገ መንግስት አንድ ኢትዮጵያዊ እንደ ዜጋ ከክልሉ ውጭ ይዞት የሚሄደው፤ በየትኛውም የኢትዮጵያ ክልል መብቴ ነው ብሎ እንዲከበርለት የሚጠይቀው መብት አልተሰጠውም።
yacob
ዶክተር ያዕቆብ ሃይለማርያም
በዚህ ምክንያት አንድ የአማራ ጎሳ ተወላጅ ዛሬ ኦሮሚያ፤ ደቡብ፤ ትግራይ፤ ሱማሌም ሆነ ቢኒሻንጉል ወዘተ ተብለው በተከለሉት የኢትዮጵያ የጎሳ ክልሎች ውስጥ እንኳን ቢወለድ አንተ የዚህ አካባቢ ጎሳ ተወላጅ ስላልሆንክና አማራ ስለሆንክ ከዚህ ወጥተህ ወደ ራስህ የአማራ ክልል ሂድ ተብሎ ሊባረር ይችላል። ዶክተር ያቆብ ሃይለማርያም ዛሬ አማራውም ሆነ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በፈለገው የኢትዮጵያ ክልል ሂዶ መኖር ይችላል ይህንንም ህገ መንግስቱ ይፈቅዳል እያለ በአሜሪካን ሬድዮ የአማርኛ ክፍል እየቀረበ ሲያስረዳ ቆይቶ አል። እውነቱ ግን ይህ አይደለም። ዶክተር ያቆብ ዛሬ በስራ ላይ የዋለው ቋንቋንና የጎሳ ማንነትን መሰረት አድርጎ የተቀረጸው ህገመንግስት መብትን ከጎሳ ማንነት ጋር በማያያዝ የአንድ ኢትዮጵያዊ መብት በጎሳ ማንነቱ ከተከለለት ክልል ውጭ እንደማይሻገር አይገልጽም። ይህን መግለጽ የጎሳን ፌዴራሊዝም አጥፊነትና አፍራሽነት ስለሚያጋልጥ የጎሳ ፌዴራሊዝም ደጋፊ የሆነው ዶክተር ያቆብ ሃይለማርያም ይህንን ጉዳይ በጭራሽ አያነሳውም። ዶክተር ያቆብ የጎሳ ፌዴራሊዝም ደጋፊ መሆኑን የሚያረጋግጥልን አንዱ ማስረጃ ከቅንጅት መፍረስ በኋላ የተመሰረተውን ህብረ-ብሄራዊ ይዘት ያለውን የአንድነት ፓርቲ በጎሳ ፌዴራሊዝም መርህ የሚያምነው የመድረክ አባል እንዲሆን የተጫወተው ከፍተኛና ቁልፍ ሚና ነው። ዶክተር ያቆብ በሚሰጣቸው የሬድዮ መግለጫዎች የዛሬው ህገመንግስት የኢትዮጵያን ዜጎች ከቦታ ቦታ ተዘዋውሮ የመኖር መብት ያረጋግጣል ሲል የዛሬው የኢትዮጵያ ህገመንግስት ዋና የማእዘን ራስ የሆነውን የአንቀጽ ስምንት ትርጉምና አንድምታ አጥቶት ወይም ዘንግቶት አይደለም።
እንደሚታወቀው መድረክ የኢትዮጵያ ህዝብ ለቅንጅት በግንቦት 1997 ዓ.ም የሰጠው ሰፊ ድጋፍ ያስደነገጣቸው የጎሳ ፌዴራሊዝም አራማጆች የመሰረቱት ስብስብ ነው። የህግ ባለሙያ የሆነው ዶክተር ያቆብ ሃይለማርያም ሊነካው የማይፈልገው ጉዳይ ዛሬ አማራው ከቢኒሻንጉልም ሆነ ከጉራ ፈርዳ የሚፈናቀልበት ምክንያት ይህ በወያኔ ህገ መንግስት ውስጥ የተሰነቀረውና አንቀጽ 8 ስር የሰፈረው የጎሳ ፌዴራሊዝም ዋና መገለጫ የሆነው ድንጋጌ ነው። ኢትዮጵያ የብሄር፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ሀገር ነች በሚል የቡድን መብትን ከግለሰብ መብት በሚያስቀድም ህገ መንግስት ውስጥ የተሰነቀረው ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ከቦታ ቦታ ተዘዋውሮ ህይወቱን ሊመራ ይችላል የሚል አንቀጽ የአንድን ኢትዮጵያዊ መብት ሊያስጠብቅ እንደማይችልና አንድ ኢትዮጵያዊም እኔ የኢትዮጵያ ዜጋ ስለሆንኩኝ መብቴ በማናቸውም የኢትዮጵያ ክፍል ውስጥ ሊከበር ይችላል ለማለት እንደማያስቸለው ያለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት ልምዶች አሳይተውናል። ባለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት ኦሮሚያ ክልል በሚባለው የኢትዮጵያ ክፍል ውስጥ የሚገኙ አያት ቅድመ አያቶቻቸው እዚያ ተወልደው ያደጉ ኦሮሞ ያልሆኑ ተወላጆች በተለይም በዚህ የኦሮሚያ ክልል ተብሎ በተሰየመው ክልል ውስጥ በስፋት የሚኖሩት የአማራ ተወላጆች እናንተ መጤዎች ስለሆናችሁ የትምህርትም ሆነ የስራ እድል አይገባችሁም፤ ቅድሚያ የሚሰጠው ለኦሮሞ ተወላጆች ነው ተብለው ከማናቸውም አንድ ኢትዮጵያዊ ሊያገኝ ከሚገባው ጥቅምና መብት ተሳታፊ እንዳሆኑ ተደርገው ኖረዋል። የሌሎችም ከኦሮሞ ጎሳ ውጭ ያሉ ተወላጆች እንደዚሁ በኦሮሞ ክልል ውስጥ በኢትዮጵያዊነት የሚገባቸውን መብት ተነፍገዋል። ይህንን ጎሳን መሰረት ያደረገ አስከፊና ጎሰኛ አሰራር ኢትዮጵያ እየተመላለሰ ለረጅም ጊዜ ቆይታን ያደረገው ዶክተር ያቆብ አይቶአል፤ ድርጊቱ ከደረሰባቸውም ሰዎች ሳይሰማ አልቀረም። ለምን ግን ይህንን የኢትዮጵያ መተዳደሪያ ሆኖ ዜጎችን የአድልዎ ስርዓት ሰለባ ያደረገ ህገመንግስት ጉልህ የሆነ ጉድለትና አጥፊነት ዶከተር ያቆብ ማየት እንዳቃተውና በህገመንግስቱ መሰረት ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወደፈለገበት የኢትዮጵያ ክፍል ሄዶ ህይወቱን ሊመራ ይችላል እያለ በአሜሪካን ድምጽ የአማርኛ ክፍል እንደሚነግረን አይገባኝም።
ለዚህም ነው ከሃያ ሁለት ዓመት ጥፋት በኋላ እንኳን ዶክተር ያቆብ ይህንን የጎሳ ፌዴራሊዝምን መሰረት አድርጎ የተጻፈውን የዛሬውን ህገመንግስት ላለመንካት፤ ለላመተቸት የፈለገው። ለነገሩ ያቆብ የሚያምንበትን የጎሳ ፌዴራሊዝምን ፍልስፍና እንዴትስ አድርጎ ይቃወም? እነ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም፤ እንደዚሁም ከአንድነት ፓርቲ ወጥተው ዛሬ የሰማያዊ ፓርቲን የመሰረቱት ወጣቶች የአንድነት ፓርቲ የጎሳን ፖለቲካ ከሚያራምደው የመድረክ ድርጅት አባል መሆን አይገባውም
ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም
ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም
ብለው በመቃወም፤ የአንድነት ፓርቲም በዚህ ጉዳይ ላይ ስብሰባ አድርጎ እንዲነጋገሩበትና እንዲከራከሩበት ሲጠይቁ፤ ዛሬ በአመራር ላይ ያሉት የአንድነት ፓርቲ መሪዎችና ዶ/ር ያቆብ ኃይለማርያም ይህንን አሻፈረን ብለውና ሽንጣቸውን ገትረው የጎሰኞች ስብስብ የሆነውን መድረክ የተባለውን ዛሬ ኢትዮጵያ በምትደዳደርበት የጎሳ ፌዴራሊዝም ስርዓት ተከታይ ቡድን ተቀላቅለዋል። በኢትዮጵያ ውስጥ እየተሰራበት ያለው በቡድን መብት ላይ የተመሰረተ ህገመንግስት ዛሬም በወያኔ ይሁን ነገ እነ መድረክ በለስ ቀንቶአቸው ስልጣን ቢጨብጡ የኢትዮጵያውያንን መብት ሊያረጋግጥ አይችልም፤ ዛሬ እየሆነ እንዳለው ኢትዮጵያን በጎሳ በታትኖ ከማፍረስ የዘለለ ዓላማና ግብ የለውም። ለምን ቢሉ ይህ ህገመንግስት መብት የሚሰጠው በጎሳ ማንነት ላይ ተመስርተው በተከለሉ ክልሎች ውስጥ ላሉ ያንድ ጎሳ ተወላጆች ሲሆን እነዚህ የአንድ ጎሳ ተወላጆችም ከእነሱ ክልል ውጭ ይዘውት ወደ ሌላ ክልሎች የሚወስዱት መብት የላቸውም። አማራው የጎሳ ፖለቲካ ሰለባ የሆነበትም መሰረታዊ ምክንያት ይህ ነው። የጎሳ ፌዴራሊዝም ዛሬ በወያኔ ትግሬዎች ዘመን እየተደረገ እንዳለው የኢትዮጵያዊነት ሀገራዊ ስሜትን የሚያፈርስ፤ ጥላቻንና ጥርጣሬን የሚያስፋፋና ለእርስ በርስ እልቂት የሚጋብዝ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር መቀጠል እንዳትችል የሚያደርግ፤ የኢትዮጵያን ህዝብ መሰረታዊ የመብትና የእኩልነት ጥያቄዎች የማይፈታ ነው። ዛሬ መንግስታዊ ስልጣን በመቆጣጠራቸው በጎሳ ፌዴራሊዝም መርህ ላይ የተመሰረተው ህገ መንግስት አተገባበር ችግር የማይፈጥርባቸው የምርጡ የትግራይ ተወላጆችና ለእንደሱ በባርነት አድረው የሚያገለግሏቸው ጥቂት የሌሎች ጎሳ ተወላጆች ብቻ ናቸው።
አንድ በኢትዮጵያ ስላለው የጎሳ ፌዴራሊዝም ጥናት ያደረገች ሎቪስ አለን የምትባል የኖርዌይ ተወላጅ  እንዳመለከተችው የኢትዮጵያን በጎሳ ላይ የተመሰረተ ፌዴራሊዝም በዓለም ውስጥ ከሚገኙ የፌዴራል ስርዓቶች ሁሉ የተለየ የሚያደርገው እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የዜግነት መብት የሚቀዳጀው በጎሳ ማንነቱ አማካይነት ብቻ መሆኑና በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ዜግነት ከጎሳ አባልነት ውጭ ሊታሰብ ያለመቻሉ ሁኔታ ነው።ዛሬ አማራው ከተወለደበት፤ አድጎና ከብዶ፤ ልጆች አፍርቶ ከሚኖርበት የደቡብ፤ የኦሮሞ፤ የሶማሊ፤ የቢኒሻንጉል ወዘተ ክልሎች እንዲወጣ የተደረገው የጎሳ ፌዲራሊዝም በደነገገው ኢ-ዲሞክራሲያዊና ፋሽስታዊ የሆነ ህገ መንግስት ምክንያት ነው። ስለዚህ ስለ አማሮችም፤ ሰለ አፋሮችም፤ የጋምቤላ ተወላጆችም፤ ወዘተ መፈናቀል ሆነ በተደጋጋሚ ባለፉት ሃያ ሁሉት ዓመታት ከትግራይ ክልል ውጭ ባሉ የኢትዮጵያ ክፍሎች ለተካሂዱት በርካታ አውዳሚ የጎሳ ግጭቶችና ፍጅቶች፤ የህዝብ መፈናቀል፤ ስደትና መከራ መንስኤ ስንነጋገር ክርክራችንም ሆነ ውይይታችን ትኩረቱን ማሳረፍ ያለበት ጥላቻና ግጭትን አራጋቢ የሆነው የጎሳ ፌዴራሊዝም ኢትዮጵያን እንደ ሀገር እንድትቀጥል የሚያደርግ ነው ወይስ አይደለም? በሚለው ጥያቄ ዙሪያ መሆን አለበት የሚል አስተያየት አለኝ። ዛሬ የፖለቲካውን መድረክ ያጣበቡት በሀገርም ሆነ በውጭ ያሉት የወያኔ መንግስት ተቃዋሚዎች (የመድረክ ቡድን አባሎች፤ አዲሱና በቅርቡ ራሱን ያስተዋወቀው የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር፤ በጄኔራል ከማል ገልቹ የሚመራው የኦነግ ክንፍ፤ ወዘተ) እንዲሁም ግንቦት ሰባትን የመሳሰሉት አዲሱን ኦነግንና የኦጋዴን ነጻ አውጭዎችን እያጀቡ በየመድረኩ ብቅ የሚሉት ጭምር የሚያራምዱትና የሚደግፉት የጎሳ ፌዴራሊዝም ኢትዮጵያን እንደ ሀገር እንድትቀጥል የማያስችል፤ ኢትዮጵያን የሚበትንና የእርስ በርስ ጦርነት አውድማ፤ የተፋፋመ ጅምላ የጎሳ ፍጅት የሚዳርግ መሆኑን ገደምም ጠመም ሳላደርግ መግለጽ እፈልጋለሁኝ። አስገራሚው ነገር ኢሳት የተሰኘው ሬድዮና ቲሌቪዥን የጎሳ ፌዴራሊዝም አራማጅ ለሆነው ለአዲሱ የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር ወደ አንድ ጎን ያደላ ሽፋን ሲሰጥ (ኢሳት ከቀድሞው የኢሰፓ ካድሬ ዛሬ ደግሞ የአዲሱ የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር አንዱ መሪ ከሆነው ከዶክተር በያን ሁሴን ኦሶባ፤ ጋር ያደረገውን ሰፊና ተከታታይ ቃለመጠይቅ ያሰተውሏል) እንደ “ነጻ የመገናኛ ብዙሃን ተቋም” ይህንን አዲሱ የኦነግ ክፍል ያነገበውንና በወያኔ የሃያ ሁለት ዓመታት አስተዳደር ስራ ላይ ውሎ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር እያፈረሰ ያለውን የጎሳ ፌዴራሊዝም የሚቃወም አመለካከት ለማስተናግድ ግን ፈቃደኛ አልሆነም። በዚህም ሳቢያ የእሳት ባለቤት የሆነው የግንቦት ሰባት ድርጀት አሻራ ከምንጊዜውም በላይ ጉልህ ሆኖአል።
ከላይ እንደ ገለጽነው ብሄር፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የሚባሉትን የወል ስብስቦችን መሰረት ያደረገው የዛሬው የኢትዮጵያ ህገ መንግስት መብት የሚሰጠው ለእነዚህ ስብስቦች እንጂ ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዜጋ አይደለም። በማናቸውም ዲሞክራሲያዊ ሀገር እንደሚታየው ሉዓላዊነት የሚሰርጸው ነጻ ከሆነው እያንዳንዱ ዜጋ ነጻ ምርጫ እንጂ ብሄር፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ከሚባሉ የማይጨበጡ ስብስቦች አይደለም።በዲሞክራቲክ መንግስታዊ ስርዓቶች ህገ መንግስት ውስጥ ተገልጾ የምናነበው ሉአላዊነት የሚሰርጸው ከእያንዳንዱ ግለሰብ ነጻ ፈቃድ ሲሆን እያንዳንዱ ነጻ ያንድ ሀገር ዜጋ ድጋፉን የሚሰጣቸው የህዝብ ተወካዮች ፓርላማ ገብተው በዚያ በተሰጣቸው የእያንዳንዱ ዜጋ ህዝባዊ ውክልና መሰረት ዲሞክራሲያዊ የህዝብ መንግስት ያቋቁማሉ። ይህም በእያንዳንዱ ዜጋ ነጻ ፈቃድ ላይ ተመስርቶ የተቋቋመ መንግስት ተጠሪነቱ ብሄር፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ለሚባሉ የማይዳሰሱና የማይጨበጡ የወል ስብስቦች ሳይሆን ለእያንዳንዱ የመምረጥ መብት ላላው ነጻ ዜጋ ይሆናል። በዚህ ዓይነት የአንድ ሀገር ሉዓላዊነት የሚሰርጸው ብሄር፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ከሚባሉ የወል ስብስቦች ሳይሆን ከእያንዳንዱ የኢትዮጵያ ዜጋ ነጻ ፈቃድ ይሆናል። የአንድ ሀገር ዜጎች በዚህ ዓይነት በየግላቸው በፈቃዳቸው በሚሰጡት ህዝባዊ ውክልና የሚመሰረት መንግስት ተጠሪነቱ ለዚያ ለመረጠው ህዝብ ስለሚሆን ይህ ተጠሪነቱ ለህዝብ የሆነ መንግስት የመረጠውን፤ በስሙም መንግስት እንዲመሰርት የወከለውን ህዝብ በደንብ ሳያገለግል ሲቀር ይህ ነጻ ህዝብ በምርጫ ድምጹን በመንፈግና ውክልናውን በማንሳት ይህንን መንግስት በሌላ የተሻለ መንግስት ሊተካ ይችላል። የዲሞክራቲክ ሀገሮች ለህዝቦቻቸው ልማትና እድገትን፤ ሰላምና ደህንነትን፤ የተረጋጋ ማህበረሰባዊና ፖለቲካዊ ህይወትን ያረጋገጡት በዚህ ዓይነት ከእያንዳንዱ ነጻ የሆነ ዜጋ ፈቃድና ምርጫ በተቋቋሙ መንግስታት እንጂ ስልጣን-ወዳድ ልሂቃን በብሄር፤ ብሄረሰቦችና ህዝቦች በሚባሉ የወል ስብስቦች ስም የዚህ ወይም የዚያ ጎሳ ወኪል ነን ብለው በህዝብ ላይ በሚጭኑት፤ ከፋፋይና የማያባራ የጥላቻና የእልቂት መንሥኤ ሊሆን በሚችል የጎሳ ፌዴራሊዝም ስርዓት አይደለም።
በዚህ ጸሃፊ እምነት ተማርኩ ነኝ ባዩ የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ክፍል ላለፉት ሃምሳና ስልሳ ዓመታት ጥናትና ምርምር ላይ ያልተመሰረቱ፤ የኢትዮጵያን ህዝብ መሰረታዊ ችግሮች ያልቃኙ ዝም ብለው በመፈክር ደረጃ የሚገፉ ሃሳቦችን (የብሄረሰብ መብት፤ የመደብ ትግል፤ ወዘተ) በኢትዮጵያ ህብረተሰብ ላይ በመጫን የኢትዮጵያን ህብረተሰብ እንደ ቤተ-ሙከራ (ላቦራቶሪ) የአውዳሚ ሃሳቦችና ድርጊቶች ሰለባ አድርጎአል። ይህ የዚህ ጽሁፍ ጸሃፊም በለጋ የወጣትነት እድሜው ለሶስት ዓመታት ኢህአፓን በጀሌነት ተቀላቅሎ ለዚህ በእንጭጭ አይምሮ ለተቀፈቀፈ አፍራሽና አውዳሚ ሃሳብ ተግባራዊነት የበኩሉን የጥፋት አስተዋጽዖ አድርጐአል። በዚህ ትውልዳችን በፈጸመው ጥፋት ከመኩራራት ይልቅ በተደጋጋሚ በአደባባይ ይቅርታም ጠይቆአል። ዳሩ ግን ይህ ያልተመረመሩና ጥናት ያልተደረገባቸውን ጎጂ የሆኑ የፖለቲካ ሃሳቦችን በማህበረሰባችን
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌና ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌና ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ
ላይ የመጫኑ አዝማሚያ ዛሬም ቀጥሎአል።፡ ቢያንስ በውጭ ሀገር በነጻው ዓለም የምንኖረው ኢትዮጵያውያን እንዲሁ በጀሌነት የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች የሚያራግቧቸውን የፖለቲካ መፈክሮች ተቀባይና እንደ ገደል ማሚቶ አስተጋቢ ደጋፊዎች ከመሆናችን በፊት የጎሳ ፌዴራሊዝም የሚባለው የፖለቲካ አስተሳሰብ ለኢትዮጵያ ሀገራዊ ፋይዳው ምን ይመስላል?፤ የጎሳ ፌዴራሊዝም አራማጅ የነበሩ የቀድሞዋን ዩጎዝላቪያና የሶቬዬት ህብረት የመሳሰሉት ሀገሮች መጨረሻ ምን ሆነ? ብለን መጠየቅ ይኖርብናል። በጎሳ ማንነት ላይ የተደራጀ አግላይ ፖለቲካ አግላይነትን ከሚጻረረው የዲሞክራሲ ጽንሰ-ሃሳብ ጋር ያለውን ርቀት መገንዘብ ያስፈልጋል። የጎሳ ፌዴራሊዝም ከዲሞክራሲ ጋር ምንም ግኑኝነት የለውም። እኔ የጎሳ ፌዴራሊዝም የዲሞክራሲም መገለጫ አይደለም ብዬ እከራከራለሁኝ እሞግታልሁኝ። እስቲ በዚህ በጎሳ ፌዴራሊዝም ዙሪያ የዚህ አራማጅ የሆኑት በርካታ በኢትዮጵያም ሆነ (የመድረክ አባሎችን ያጠቀልላል) ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ በጎሳ ማንነት ላይ በተመሰረተ የፖለቲካ ስርዓት የሚያምኑ ወገኞች በአደባባይ ክርክር ያድርጉበት። የጎሳ ፌዴራሊዝም እኔ የኢትዮጵያ ህዝብ ብዬ ለምጠራው፤ የጎሳ ፌዴራሊዝም ደጋፊዎች የኢትዮጵያ ህዝቦች ብለው ለሚጠሯቸው ኢትዮጵያውያን ለምን እንደሚበጅ ወይም እንደማይበጅ ቢያንስ ከሃያ ሁሉት ዓመታት የጋራ ጥፋት በኋላ ውይይትና ክርክር ሊደረግበት ይገባል ብዬ እሞግታለሁኝ፤ እከራከራለሁኝ። ይህንንም ክርክር እነዚህ የጎሳ ፌዴራሊዝም አራማጆች እና ደጋፊዎች በብልጠት እንደሚያደርጉት ወደፊት የኢትዮጵያ ህዝብ የስልጣን ባለቤት ሲሆን ይወስነዋል የሚለውን ማታለያቸውን ትተው ዛሬ ገና እነሱ ወደ ስልጣን ሳይወጡና የኢትዮጵያን ህዝብ እንደ ወያኔ ትግሬዎች የጭቆና ቀንበር ሳይጭኑበት በአደባባይ ሃሳባቸውን ህዝብ በተሰበሰበበት መድረክ ወጥተው ለከራከሩበት ይገባል። ይህ በየመድረኩ ለፖለቲካ ተቃዋሚዎች የሚያጨበጭበው በስደትም ሆነ በሀገር ቤት የሚኖር ህዝብ ቢያንስ አማራጭ እንሰጥሃለን ብለው ድጋፉን የሚሹትን ተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች ስለ ትልማቸውና አንግበውት እንታገልለታለን ስለሚሉት የጎሳ ፌዴራሊዝምን መሰል አጀንዳ ጥያቄዎችን መጠየቅ አለበት። የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው በሚል የሞኞች ብሂል ወያኔን የተቃወመ ሁሉ ወዳጄ ነው አማራጭ ይሆነኛል ማለትን ማቆም አለበት። የጎሳ ፌዴራሊዝም  የአንድ የባለ-ብዙ ጎሳዎችና እምነቶች ባለቤት ለሆነች ኢትዮጵያን ለመሰለች ሀገር አይረባትም ብዬ በጽኑ ከሚያያምኑት ሰዎች መካከል ነኝ። በዚህም ጉዳይ የመድረክን አባሎች ከመሳሰሉት የጎሳ ፌዴራሊዝምን ጠቃሚነት ከሚሰብኩ ወገኖች ጋር በሃሳብ በአደባባይ በአካልም ሆነ በጽሁፍ ወጥተን፤ ጸሃይ እየሞቀን፤ ሰው እያያን እንድንከራከርበት በትህትና እጠይቃለሁኝ።
በዚህ በጎሳ ፌዴራሊዝም ጉዳይ ላይ ህዝብ የተሳተፈበት ግልጽ ክርክር በአደባባይ እንዲካሄድ ቢያንስ በነጻው የምእራቡ ዓለም የሚኖረውና በየጊዜው ስብሰባ እየተጠራ ስለሀገሩ ጉዳይ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ ነን የሚሉ ወገኖችን የሚያዳምጠውና የሚደግፈው ኢትዮጵያዊ መጠየቅ ይኖርበታል። ይህ ግልጽ የሆነ ክርክር እንዳይካሄድ ባገር ቤትም ሆነ በውጭው ሀገር አልተቻለም። ያ የኢትዮጵያ ተማሪዎችና የግራው እንቅስቃሴ ውላጅ የሆነው ጸረ-ምሁራዊ ልማድ ዛሬም ድረስ ቀጥሏል። የተለያዩ አመለካከት ያላቸውን ወገኖች ባንድ መድረክ ላይ አቅርቦ ሃሳባቸውን ለህዝብ እንዲያቀርቡ ማድረግ እስካሁን ተቀባይነትን አላገኝም። ከዚያ ይልቅ በደጋፊዎች የታጀበ፤ የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች ነን የሚሉ ወገኞች የራሳቸውን ሀሳብ (በሞኖሎግ መልክ) ብቻ ተናግረው የሚሄዱበት፤ የእነሱን ሃሳብ የሚቃወሙ ድምጾች በስልት የሚታፈኑበት ከዚያው ከግራው ፖለቲካ የቀጠለ አሰራር ቀጥሏል። በዚህ በምእራቡ ዓለም በስደት ያለነው ኢትዮጵያውያን እንኩዋን በተቃዋሚዎች ስብሰባ ላይ እየተገኘን ያንድን ወገን ድምጽ እየሰማን ከማጨብጨብ በስተቀር የፖለቲካ ድርጅቶች ለሀገርና ለህዝብ ይጠቅማሉ ብለው የሚያራምዿቸው ሃሳቦች በአደባባይ ክርክር እንዲደረግባቸው ተጽዕኖ ማድረግ አልቻልንም። በቅርቡ የቀድሞው የወያኔ ካድሬ፤ የዛሬው የግንቦት ሰባት ዋና ጸሀፊ አንዳርጋቸው ጽጌ ዋሽንግተን ላይ ሆኖ ካለአንዳች ሃፍረትና ይሉኝታ የኢትዮጵያ የነጻነት ትግል በኤርትራ ህዝብና መንግስት እየተረዳ ኢትዮጵያን ነጻ ሊያወጣ እንደሚችል ተረት ሲነግረንና ሊያሳምነን ሲሞክር እዚያ ተሰብስበው የሚያዳምጡትና የሚያጨበጭቡለት ወገኖች ክቅርብ ታሪካችን ምን ተማሩ? ብዬ እንድጠይቅ አድርጎኛል። አንዳርጋቸው እንደማናቸውም ዓይነት ህሊና እንደሌለው ሳይካትሪስቶች ሳይኮፓቲክ ፐርሶናሊቲ እንደምንለው መዋሸት፤ መቅጠፍ ለህሊናው አይከብደውም፤ ህሊናውን አይቆረቁረውም።
አሳዛኙ ነገር የኢትዮጵያ ፖለቲካ ትላንት መንግስቱ ኃይለማርያምን፤ መለስ ዜናዊን ዛሬ ደግሞ አንዳርጋቸውን የመሳሰሉ ሳይኮፓቲክ (ህሊናቢስ የሆነ ተክለሰውነት ያለው፤ መቅጠፍ መዋሸት የማይሰቀጥጠው፤ ሰው ማለት ነው) ግለሰቦች መፈነጫነት ምቹ ሜዳ መሆኑ ነው። ይህ ኢትዮጵያውያን ልናጠናው የሚገባን አሳሳቢ ብሄራዊ ችግር ነው። የዛሬ ሃያ ሁለት ዓመት ከወያኔ ትግሬዎች ጋር ሆኖ ኢትዮጵያን በመቆጣጠር እንደ ማናቸውም የወራሪ ጦር የኢትዮጵያን ግማሽ ሚሊዮን ጦር ከነቤተሰቡ የበተነውን፤ ትጥቃቸውን ፈተው እጃቸውን በሰላም የሰጡ አራት ሽህ የኢትዮጵያ መኮንኖችን ካለአንዳች ርህራሄ የፈጀውን ሻቢያን፤ የወርቅ ጥርስ ሳይቀር ነቅሎ ከሁለት መቶ ሺህ በላይ ቁጥር ያላቸውን ኢትዮጵያውያንን ከኤርትራ ያባረረውን ሻቢያን፤ እስከ ባድሜ ጦርነት ድረስ ከወያኔ ትግሬዎች መንግስት ጋር ሆኖ የኢትዮጵያን ሃብት እንደ ጠላት ንብረት ሲዘርፍና ወደ ኤርትራ ሲያሸሽ የነበረውን ሻቢያን፤ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ አውታሮችን ተቆጣጥሮ ሲመዘብር የነበረውን ሻቢያን፤ በቅንጅት ድል ማግስት ኬንያ (ናይሮቢ) እና ሆላንድ (ዩትሬክት ከተማ ላይ) ከእነ ኦነግ ጋር በመመሳጠር አላያንስ ፎር ዲሞክራሲ (ኤፍዲ) በሚል ስም የኢትዮጵያን ህዝብ የምርጫ ውጤት ለመንጠቅ የሞከረውን ሻቢያን እኩይ ድርጊት የኢትዮጵያ ህዝብ ፈጽሞ አይረሳም። መርሳትም የለበትም።
ትላንትም ዛሬም የኢትዮጵያን ህዝብ ጠላቶች በጎሳ እያደራጀ የሚያሰማራው ሻቢያ፤ ዛሬ በወያኔ ግፍና ጎሰኛ አገዛዝ ተማረው ወደ ኤርትራ የሚገቡትን የኢትዮጵያ ወታደሮች በጎሳ እየለያየ (አማራ፤ ኦሮሞ፤ አፋር፤ ሶማሊ፤ ሲዳማ ወዘተ እያለ) የሚከፋፍለው ሻቢያ ለኢትዯጵያ በጎ ነገር ያስባል ብለው የግንቦት ሰባት መሪ ካድሬዎች ሊያሞኙን ሲሞክሩ ምን ያህል የኢትዮጵያውያንን የማሰብ ችሎታ ዝቅ አድርገው እንዳዩት ያሳየኛል። የግንቦት ሰባት መሪ ካድሬዎች (አንዳርጋቸውም ሆነ ብርሃኑ ነጋ፤ ወዘተ) እነሱ በማይቆጣጠሯቸው የህዝብ መድረክ ላይ ቀርበው ሌሎች የእነሱን ሃሳብ ከሚቃወሙ ወገኖች ጋር መድረክ በመጋራት የያዙትን አቋም ለማቅረብ ድፍረቱም ሆነ ችሎታው እንደሌላቸው አውቃለሁኝ። ነገር ግን ዛሬ በሞኖፓል በሚቆጣጠሩት የኢሳት ሬድዮና ቴሌቭዥን አማካይነት በአእምሮ ችሎታቸው ዝቅ ያሉ ወገኖችን ሊያሞኙ ይችሉ ይሆናል። እንኳን ሻቢያ ይቅርና ኤርትራ የሚባለውን የጣሊያን ቅኝ ገዢዎች የፈጠሩትን የባርነት መገለጫ የሆነውን አዲስ ጸረ-ኢትዮጵያ ማንነት የተላበሱ ወገኖች ምንጊዜም ለኢትዮጵያ በጎ እንደማያስቡና እንደማይተኙላት አንባቢ ልብ እንዲል ይህ ጸሀፊ አበክሮ ያሳስባል። አንድ ስለ ኤርትራ ብሄረተኞች ሰፊ ጥናት ያደረገ ኢትዮጵያዊ የታሪክ ምሁር ባንድ ወቅት እንዳለው “ውሃ ጠማኝ ተብሎ መርዝ አይጠጣም”።እንደዚሁም ዛሬ በወያኔ ትግሬዎች ጎሰኛ ስርዓት የተበሳጨ የጠላቴ ጠላት በሚል የሞኝ ብሂል ምንጊዜም ጠላትነቱን ለማይተወው የሻቢያ ኤርትራ ልቡን ሊሰጥ አይገባም። ወደፊት ይህንን የኤርትራን ማንነትና ጉዳይ አስመልክቶ ሌላ መጣጥፍ ለማቅረብ አስባለሁኝ። በዚህ ጽሁፌ ውስጥ ስማቸው የተጠቀሱት ግለሰቦች ወይም የድርጅት ወኪሎች፤ መሪዎች ያነሳኋቸውን የተቃውሞ ነጥቦች አስመልክቶ የሚኖራቸውን አስተያየት ለማስተናገድ፤ አስፈላጊም ከሆነ በማንኛውም መድረክ ላይ ቀርቤ ለመከራከር ዝግጁ መሆኔን በትህትና አሳውቃለሁኝ።
አሰፋ ነጋሽ *

No comments:

Post a Comment