Monday, February 3, 2014

ህወሓት ከመለስ ጋር አብሮ ተቀብሯል

ከነፃነከነፃነት አድማሱ

ይህ የያዝነው ወርሓ ለካቲት “የህወሓት ልደት የትግራይ ህዝብ ልደት ነው፣ ህወሓት ብቸኛ የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጪ ነው፣ የትግራይ ህዝብ ታሪክ ከደደቢት ይጀምራል፣ የህወሓት አላማና ፍላጎት የትግራይ ህዝብ አላማና ፍላጎት ነው፣ የትግራይ ህዝብ ከህወሓት ሌላ አማራጭ የለውም ዙሪያው ሁሉ ገደል ወይም ጠላት ነው፣ በአጠቃላይ የትግራይ ህዝብ ህልውና ከህወሓት ህልውና ጋር የተቆራኘና ድርጅቱ ስልጣን ላይ ሲኖር ትግራይም የምትኖር ድርጅቱ ከጠፋ ወይም ስልጣን ላይ ከሌለ ደግሞ የትግራይ ህዝብም አብሮ የሚጠፋ ነው”……..እያሉ በመስበክ በሰማእታት መቃብር ላይ ቆሞው የውሸት ድራማ የሚሰሩበት፣ በትግራይ ህዝብ ደምና አንጡራ ሃብት ላይ የሚነግዱበት፣ በድምሩ “ጆሮውን ቆርጠው የሰጡት ውሻ ሥጋ የሰጡት ይመስለዋል” እንዲሉ የትግራይ ህዝብ ብሄራዊ ክብሩ፣ ዳር ድንበሩንና ብሄራዊ ጥቅሙን ለባዕድ ሽጠው ሲያበቁ ነፃ አውጥተናሃል!! ልማት አምጥተንልሃል!! እያሉ የሚዘምሩበትና የሚመፃደቁበት የካቲት 11 በዓል እየመጣ ነው። ይህ ዓይነቱ ጭፍን ፕሮፓጋንዳ መርዝ ደግሞ ዛሬ የመጣ ባህል አይደለም። ህወሓት ከተፈጠረበት ቀን አንስቶ እስካሁን ድረስ ለአርባ ዓመታት ያህል ለጀሮ
እስከሚሰለች ድረስ በካድሬዎቹ አማካይነት ነጋ ጠባ በዚያች በተቀደሰች ምድር ትግራይ በአሁኑ በሃያ አንደኛ ክፍለ ዘመን የሚሰበክ የደደቢት የአደንቁረህ ግዛ ፍልስፍና መሆኑን ተራ የገጠር እረኛም ሳይቀር ያውቀዋል።Tigray People Front, TPLF
ይሁን እንጂ ህወሓት ከድርጅትነት ወደ ቡድናዊ አምባ ገነንነት፣ በኋላም ከቡድናዊ አገዛዝ ወደ ፍፁም የቤተሰባዊ መዝርፊያና የማፈኛ የግል ኩባንያ ሆኖ ከተሸጋገረ ወዲህ እኖሆ ዓሰርቱ ዓመታት አስቆጥሯል። በመጨረሻም “ጊዜ ዳኛ ታሪክ ምስክሩ ነውና” ድርጅቱ ከባለቤቱ ከቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ጋር አብሮ ግብኣተ መሬት ገብቷል። ላይመለስ አብሮ ተቀብሯል። አሁን ያለው “በድርቆሽ የተሞላ ህይወት የሌለው የቆዳ ግሳንግስ ወደ(ዓርሲ)” ተለውጦ ባንድ በኩል በአቶ ስብሓት ነጋ የ80 ዓመት ጎበዝ አለቃ የሚመራ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በኤርትራውያን የሚገፋ አሮጌ ጋሪና በወታደር የሚጠበቅ የደረቀ ሬሳ ሆኖ ቀርቷል” የሚሉ ብዙዎች በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ናቸው።
ይህ ምን ያህል እውነትነት አለው? አንድ የፓለቲካ ድርጅት ሞቷል ወይም ህይወት የለዉም ሲባልስ ምን ሲሆን ነው? ህወሓት ከበረሃ ጀግንነት ወደ ዱር አራዊትነት የተቀየረበት ጊዜስ መቼ ነው? እውነት የጥቂት ወሮ-በላና ከሃዲ መሪዎች በረሃ የገቡበትን ቀን የታላቁ የትግራይ ህዝብ ልደት ነውን? የትግራይ ህዝብ ከሌላው ሰማንያ ሚሊዮን የኢትዮጵያ ህዝብ ምን የተለየ ጥቅም ስላገኘ ነው የአንድ መርሲነሪ የፓለቲካ ድርጅት ልደት የህዝቡን ብሄራዊ በዓል ተደርጎ የሚያከብረው? ለመሆኑ የትግላችን ውጤት ነው እየተባለ የሚነገርለት ሕገ መንግስት እውነት ለትግራይ ህዝብ ይመለከተዋልን? የሚሉና ሌሎች ተዛማጅ ጥያቄዎችን እንድንመልስ ግድ ይለናል።
ወደ ዋናው የጥያቄው መልስና አርእስተ ጉዳይ ከመግባቴ በፊት ግን ለአንባቢዎቼና ለነፃ ሚዲያ ደንበኞቼ በአክብሮት የምጠይቀው በዚሁ ፅሑፍ ዙሪያ በመቃወምም ሆነ በመደገፍ ከቂም በቀል፣ ከስሜታዊ አስተሳሰብ፣ ከጭፍን ደጋፊነት፣ በአጠቃላይ የግለ ስብእና፣ የሃሳብ ነፃነትና
ሰብኣዊ መብት በማይጋፋ መልኩ በዋናው ጉዳይ ላይ ያተኰረ ክርክር ወይም ሃሳብ ቢያቀርቡ ለመማማርና በቂ መልስ ለመስጠት ዝግጁ መሆኔን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለፅ እወዳለሁ። ፍርሃትን አስወግዶ የህሊና ባርነትን ሰብሮ በመውጣት የሀገርና የህዝብ ወገን ሆኖ መከራከር፣ ለሃቅ መመስከርና በፅናት መቆም ምንኛ ያኰራል!!!
በዘመነ መሳፍንት አንዲት የጎጃም አልቃሽ ““ጎጃሜ ቡዳ ነው ቡዳ ነው ስትሉ ስትሉ አላየህም ወይ ትግሬ እርስ በርስ ሲባሉ” ብላ ተናግራለች” በማለት ከዛሬ አስራ አንድ ዓመት በፊት የህወሓት አመራር ለሁለት ተሰንጥቆ ሲፈረካከስ ያዩ አንድ አዛውንት ያለፉትን የትግራይ ባላባቶችና መሳፍንቶች ታሪክ ከህወሓት ታሪክ ጋር በማነፃፀር እንደዋዛ አጫውተውኝ እንደነበር አስታውሳለሁ። በሌላ መልኩ ደግሞ ስለ ህዝቡ ጀግንነት፣ ጨዋነት፣ ታጋሽነትና አትንኩኝ ባይነት እያስታወሱ የዛሬው ትውልድ ግን ሐሙት የፈሰሰ እንዲሁ ወኔው ተኰላሽቶ መቅረቱ በጣም ያሳዘናቸው መሆኑን በቁጭት ገልፀውልኛል። ነገር ግን በወቅቱ የነገሩኝን ሁሉ ብዙም ልብ አላልኩትም ነበር። በኋላ ግን ስለ ህወሓት የተፃፉ መፃሕፍቶች በተለይም የቀድሞ የህወሓት ታጋይና አታጋይ የነበሩት አቶ አስገደ ገብረ ስላሴ የፃፉትን ጋህዲ በሚል ሶስት ተከታታይ መፃሕፍቶችን ሳነብ “ማየት ማመን ነውና” የትግሉ ባለቤትና የድርጅቱን መስራች የነበሩት ሰዎች እንኳን ሳይቀር የመሰከሩለት ህወሓት ከተፈጠረበት ቀን ጀምሮ እስካሁን ድረስ ተግባሩ ሲመረመር ከላይ አዛውንቱ የነገሩኝ አባባል በትክክል የሚገልፅ መሆኑን ለመረዳት ችያለሁ።
“የህወሓት ታሪክ የርስ በርስ መላላት፣ ህዝብ ለህዝብ የማናቆርና ሀገርን የማፍረስ ታሪክ ነው” ቢባል ከእውነት የራቀ አይደለም። ይህን በሚመለከት ዝርዝሩን ለታሪክ ፃፊዎች ትቼ አንድ ሁለት አብነቶችን ብቻ ልጥቀስ። ህወሓት ከትጥቁ ትግል ዘመን ጀምሮ እስካሁን ድረስ ለ40 ዓመታት ያህል የዘለቀው አንድ ገዢ መፈክር ነበረው። እሱም “ የቻለ ይሩጥ!! ያልቻለ ያዝግም!! ያበቃለት ይለይለት!!? በትግርኛ (ዝኻኣለ ይጉየ! ዘይካኣለ ይሳለ! ዘብቀዐ ይታኣለ) የሚል ነው። ከመፈክሩም ጎን ለጎን በድርጅቱ የኪነት ቡድን የተሰራ ከአቶ መለስ መልክ ጋር የሚመሳሰል ፊት ለፊቱ ደግሞ ጣቱን ወደ ሰዎች ቀስሮ የሚያስፈራራ ሥዕል በየስብሰባውና ታጋዮች ባሉበት ሁሉ የሚለጠፍ ነበር።
ስዕሉ በጋሃድ በአደባባይ መውጣት የጀመረው ደግሞ ልክ እነ ዶ/ር አረጋዊ በርሄና አቶ ግደይ ዘርኣፅዮን ከድርጅቱ ተለይተው ከወጡ በኋላና “ማርክሰ ሌኒስት ሊግ ትግራይ (ማሌሊት)” ከተመሰረተ አንድ ዓመት ባልሞላ ውስጥ ነበር። ስዕሉ ያልተለመደ ነገር ስለነበረ ብዙ ታጋዮችን በተለይም ያልተማሩ የገበሬ ልጆች የሆኑትን ታጋዮች ግራ አጋብቷል። አንዳንድ ቦታም ሌሊት በሳንጃ እየቀደዱ ይጥሉት ነበር። ከጊዜ በኋላ ግን ስዕሉ ተለመደ። የሚገርመው ግን በወቅቱ የድርጅቱን የኪነ ጥበብ አባል ሆኖ ስዕሉን ያቀነባበረ ሳኣሊውንም ጭምር ከጥቂት ወራት በኋላ ድርጅቱን ለቆ በመውጣት ዛሬ በስደት ዓለም በህወይት ይገኛል። ስሙን ያልጠቀስኩበት ምክንያት ደግሞ የሱ ፍቃደኝነት መጠየቅ ስላለብኝ ነው። የመፈክሩ ዋና አላማና ስትራተጂም የሚከተሉትን ሶስት ዋና ዋና ነገሮችን ያቀፈ ነው፡-
1. አንደኛ የአቶ መለስ ዜናዊና የአቶ ስብሓት ነጋ ቡድን ተቀናቃኝ ወይሞ ሞጎደኛ ተብለው የሚጠረጠሩትን ያመራር አባላት፣ ምሁራንና የጦሩ አለቆችን (ይህችን ባቄላ ካደረች አትቆረጠምም) በማለት ቀስ በቀስ የማፅዳት ስልትና ስትራተጂ ነው። ይህንንም ሰሞኑን በኢትዮ- ሚዲያ ድሕረ ገፅ የወጣውን የነ ሙሴ፣ ዶ/ር አታክልት፣ ገሰሰው አየለን ጨምሮ ተኩሉ ሃዋዝ፣ መለስ ካሕሳይ፣ ዶ/ር አረጋዊ በርሄ፣ ግደይ ዘርኣፅዮንና ሌሎች በሽዎች የሚቆጠሩት የድርጅቱን ከፍተኛና መካከለኛ የአመራር አባላትን ያካትታል።
2. ሁለተኛው የመፈክሩ አላማና ስትራተጂ የትግራይ ብሄረተኝነትንና ብሎም የኢትዮጵያዊነት ስሜትን ከትግራይ ምድርና ከህዝቡ አስተሳሰብ ከስረ መሰረቱ በመፋቅና በማጥፋት በምትኩ በትግራይ ብሎም በሀገራችን የኤርትራ ሻዕቢያዊ አመለካከት የበላይነት እንዲይዝ ማረጋገጥ ነው። በዚሁ ዙሪያ በቅድሚያ የተመቱት የድሮ አስተሳሰብ፣ ሀገራዊ ስሜትና እንዲሁም በኤርትራ ጉዳይና በአገር አንድነት ጉዳይ ላይ የከረረ አመለካከት አላቸው ተብለው የሚገመቱትን ባላባቶችንና የሀገር አዛውንቶችን ናቸው። ቀጥሎም የተመቱት የትግራይ መሁራኖች ናቸው። በኤርትራና በሀገር ጉዳይ ዙሪያ የሚከራከሩና ጥያቄ የሚያነሱ ምሁራን እንደ ኤለክትሪክ ይፈሩዋቸው ነበር። በዚህ መሰረት “ሽዋውያን ተጋሩ” የሚል የቅፅል ስም መለጥፍ ብቻ ሳይሆን በዘፈንም ሳይቀር ቅስማቸው እንዲሰበርና አንገታቸው እንዲደፉ ተደርጓል። በዚህ ምክንያት የቻሉትን ከድርጅቱ ሸሽተው እንዲያመልጡ ያልቻሉት ደግሞ ለእስርና ለግድያ ተዳርጓል። በዚህ ምክንያት በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚኖሩ የትግራይ ምሁራን ዛሬም ስለህዝባቸውና ሀገራቸው ጉዳይ ደፍረው ጥያቄ እንዳያነሱ ፍርሃት እንደ ወባ
በሽታ በደማቸው ውስጥ ገብቶ እያዩ እንዳላዩ ዝም እንዲሉ ትልቅ ምክንያት የሆነውን ጠባሳ እስካሁን ድረስ አልሻረም።
ዛሬ በአረና ትግራይ አባላትና ደጋፊዎቻቸው እየደረሰ ያለው ዱላም ከዚሁ የተለየ አይደለም። ለአንድ የአረና አባል ከአምስት በላይ ሰላዮች በመመደብ ኮቲያቸውን እየተከተሉ መውጫና መግቢያ ያሳጧቸዋል። ዛሬ ትግራይ ለነ ስብሓት ነጋና ሌሎች መሪዎች ታማኝ የሆኑትን የኤርትራ ተቃዋሚ ነን የሚሉ ድርጅቶች በነፃነትና በልበ ሙሉነት የሚንቀሳቀሱባት በአንፃሩ ከህዝቡ አብራክ የተፈጠሩ ለነ አረና ትግራይና ሌሎች ሀገር በቀል ድርጅቶች ግን በገዛ ሀገራቸው ተሸማቅቀውና በአደባባይ በዱላ እየተመቱ የሚኖሩባት ምድራዊ ሲኦል ሆና ትገኛለች።
በመሆኑም ዛሬ ሰፊው የትግራይ ህዝብ ባንድ በኩል የትግራይ ሻዕቢያ በሌላ በኩል ደግሞ የኤርትራ ሻዕቢያ አጣብቅኝ ውስጥ ገብቶ በሁለት አለንጋ እየተገረፈ የሚገኝ ህዝብ ሆኗል። ታዲያ!! ለዘህ ሚስኪን ህዝብ አለሁልህ የሚል ወገን ማን ይሆን?
3. ሶስተኛው የመፈክሩ አላማና ስትራተጂ በህዝቡ የስነ ልቦናና የአካል ጥቃት በማድረስ በተለይም በትግራይ ምድር ፍርሃት፣ ሽብር፣ ጥርጣሬና ህወከት በማንገስና የህዝቡን ሁለንትናዊ አስተሳሰብ በመቆጣጠርና በማደንዘዝ ፀጥ ረጭ ብሎ እንዲገዛና ለጥቂት መሪዎች ዘላለማዊ ስልጣን አገልጋይ ሆኖ እንዲኖር ለማድረግ ነው። በሌላ አነጋገር ትግራይ ወፍ እንኳን ዞር የማይልባት፣ ሌላው ኢትዮጵያዊ በትግራይ ህዝብ ጉዳይ ላይ እንደማያገባው ተደርጎ መፈናፈኛ በማሳጣት በስመ ልማት እንደፈለጉ የሚግጥዋት የህወሓት የጓሮ አትክልት ሆና እንድትኖር ለማድረግ ነው።
ልበ በሉ!! የትግራይ ህዝብ በጦርነት የደቀቀ ህዝብ ነው። ትግራይ ደርግ፣ ኢዲዩ፣ ጀብሃ፣ ሻዕቢያ፣ ኢሕአፓ፣ ህወሓትና ሌሎች ብረት ያነገቡ ሀይሎች የሚንቀሳቀሱባት ለአስራ ሰባት ዓመታት ያህል የጦርነት አውድማ ሆና ቆይታለች። ዛሬም ህዝቡ ከጥይት ጭኾት አልተላቀቀም። በኤርትራና በኢትዮጵያ በሁለቱም ሀገሮች ድንበር ከሩብ ሚሊዮን በላይ ሰራዊት በመሸገበትና በተፋጠጠበት የጦርነት ደመና ስር ሆኖ ዛሬ ነገ ውጊያ ይጀመራል እያለ በፍርሃት ተውጦ የሚገኝ ህዝብ ነው። በዚህም ላይ በየጊዜው ከያሉበት በታጣቂዎች እየታፈኑ ወደ ኤርትራ ተወስደው ደብዛቸው የማይታወቁ ንፁኃን ዜጎች ቁጥራቸው ቀላል አይደለም። በዚሁ ፍርሃት ቀያቸውንና ቤታቸውን እየለቀቁ ወደ ዓረብ ዓለም የሚሻገሩና ወደ ማሀል ሀገር በመሸሽ የኢትዮጵያ ዋና ዋና ከተሞችን በልመና ያጥለቀለቁት የየተኛው አካባቢ እንደሆኑ ማንም ኢትዮጵያዊ ያውቃል። እነዚህ ግጭቶችም እንደ ፓለቲካ መሳሪያና ማስፈራሪያ እየተጠቀሙ “እኛ ከሌለን ያ ሁሉ
ጠላት ይመለሳል፣ ሻዕቢያ ተመልሶ ይውጥሃል፣ ኦነግና ትምክሕተኞች ቂማቸው ይወጡቡሃል፣ የሽብርተኞች ዒላማ ትሆናለህ፣ በትግራይ የተተከሉ ፋብሪካዎች ተነቅለው ወደ ማሃል ሀገር ይወሰዳሉ፣ በትግልህ የቀበርካቸው ጠላቶች ከመቃብር ተነስተው ይመጣሉ፣ ወዘተ እያሉ ነጋ ጠባ ህዝቡን ማሸበርና ማደንቆር የተካኑበት ዋነኛ የአገዛዝ ጥበባቸው ሆኖ ይገኛል።
ወንድሞቼ ሆይ!! ታዲያ እንዲህ ዓይነቱ የቆሸሸ ታሪክ ያለው ድርጅት ዛሬ በትግራይ ህዝብና በተለይም በአረና አባላትና ደጋፊዎቻቸው ላይ የአራዊት ስራ ቢሰራ የሚያስገርም አይደለም። ህዝብን ሁሉ ጊዜ ማታለል የማይቻል መሆኑን ያልገባቸውና ጊዜውም ጥሏቸው እየሄደ መሆኑንም የማይቀበሉ እንደ ሾላ ፍሬ ውስጣቸው የበሰበሱ መሪዎች እስከ ህልፈተ ቀናቸው ድረስ “የደንቆ ልቅሶ መልሶ መላልሶ” እንዲሉ ዛሬም የሚናገሩት ቋንቋና የሚሰሩት ስራ ያው በጫካ የለመዱት ዓይነት ነው። ከላይ የተጠቀሰው የመፈክራቸው አላማና ስትራተጂም በትክክል ሲተረጎም “እምቢ ያለ ሰው ጥይት አጉርሰው” ከሚለው የደርግ ስርዓት መፈክርና ተግባር ጋር አንድ ዓይነት መሆኑን የኢትዮጵያ ህዝብ ይስቷል ብዬ አልገምትም።
የሚያሳዝነውና የሚያስገርመው ነገር ግን ትግራይን የጥፋትና የመከራ ሞዴል በማድረግ የሚፈፅሙትን ጉድ እንደ ኤይድስ ወረርሽኝ በሽታ ወደ ሌሎቹ ክፍላተ ሀገራትም እየተዛመተ መምጣቱ ነው። በዚሁ ነጥብ ዙሪያ በቀጣዩ ፅሑፌ ተመልሼ እመጣለሁ። ቸር ሰንብቱ።
http://ecadforum.com/Amharic/archives/10902/

No comments:

Post a Comment