Thursday, February 27, 2014

የኢትዮጵያ አየር መንገድ እና …

(ይድነቃቸው ከበደ)

ealines


“የኢትዮጵያ ሃየር መንግድ ለአፍሪካ ኩራት ነው” ሲባል ከቃላት መፈክርነት ባለፈ የአውነትም ኩራት ስለመሆኑ ጥርጣሪ  የሚያድርባቸው ዜጎች እንደሚኖሮ እገምታለው፡፡ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ አየር መንግድ በረዥም ታሪኩ ውስጥ ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች በአንፃራዊነት በተቋሙ ውስጥ ስማቸው እጅግ የገነነ ብቁ አብራሪዎች፣ የቴክኒክ ባለሙያዎች (ግራውንድ ቴክኒሻን) እና ድጋፍ ሰጪ ሰራተኞች በአብዛኛው በኢትዮጵያዊያን የተሞላ ነው፡፡ ለዚህም ነው የአፍሪካ ኩራት ለመባል የበቃው፡፡ ይህ ኩራት እና አድናቆት ከታላቁ አፍሪካዊ የነፃነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ ጀምሮ ጥቂት በማይባሉ አፍሪካዊያን ዘንድ ተቀባይነት ያገኘ ነው፡፡
በተጨማሪም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሎሜ፣ማላዊ እና ቶጎ በመሳሰሉ የአፍሪካ አገሮች ከፍተኛ አክሲዮን ሼር በመግዛት እያስተዳደረ እና እያንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ እንዲሁም የተለያዩ የአፍሪካ አገር ተወላጆች በአብራሪነት እና በቲክኒሻንነት እያሰለጠነ ይገኛል፡፡ ይህ ደገሞ አየር መንገዱ በበለጠ በአፍሪካ እና በተቀሩት የዓላም አገራት ተቀባይነት ለማግኘት የሚያስችሉት መልካም ተግባራቶች ናቸው፡፡ እንዲ አይነቱ ለውጥ እና እድገት ለአገር ኩራት ስለመሆኑ ጥርጣሪ የሚያሳድር አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ ከላይ የተገለፁት የአየር መንገዳችን መልካም ስራዎች በተቋሙ ውስጥ ለሚታዩ የአስተዳደር ችግሮች እና አየር መንገዱ ሊደርስበት ይገባው ለነበረ የእድገት ደረጃ አለመድረስ ምክንያቱ ምን እንደሆነ እና መሰል አሳቦችን አንስቶ ለመወያየት ብልጭ ድርግም የሚለው የአየር መንገዳችን እድገት የአሳብ ፍጭት ለማድረግ የሚገድብ አይደለም፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታ የኢትዮጵያ አየር ኃይል የራሱ የሆነ ድንቅ ታሪክ ያለው ነው፡፡ የአየር ኃይል ካፒቴኖቻችን እንደ ንስር አሞራ ከሰማይ ወደ ምድር በሚገርም ብቃት በመብረር ጠላትን እና የጠላት ሠፈርን አመድ በማድረግ የሚታወቁ ናቸው፡፡ እንዲህ አይነቱ ግርማ ሞገስ ያለው የአገር ኩራት የሆነው ተቋም እና ተቋሙ ያፈራቸው ባለሙያዎች በወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ቀጥተኛ ትዕዛዝ ለመፍረስ በቃ እንጂ፡፡ ተቋማትን አፍርሶ እንደ አዲስ መገንባት አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት የስርዓቱ ዋንኛ መገለጫ ነው፡፡ ለዚህም ነው ሁሉ ነገር እንደአዲስ የመጀመር መርዘማ የሆነ የኋላ ጉዞ ሙጥኝ ብለው የተያያዙት፡፡ የሰዎቹ አደገኝነት የሚጀምረው ኢትዮጵያ የምትባል አገር እንደ አገር መታየት ከጀመረች መቶ ዓመት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ነው ብለው የነገሩን ዕለት ነው፡፡ በዚህም መሠረት የኢትዮጵያን አየር ኃይል በማፍረስ አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት በአዲስ መልክ እንዲቋቋም ያደረገ ሲሆን፣ በዚህም ምክንያት እጅግ በጣም ድንቅ የሆኑ የአየር ኃይል ካፒቴኖቻችን ከአገር ለመሰደድ ተገደዋል፡፡
እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት የአንድ ሳንቲም ግልባጭ የሆኑት የኢትዮጵያ አየር መንገድ እና አየር ኃይል ካፒቴኖቻችን ሽሽትና ምክንያት እንዲሁም ውጤት በአጭሩ ለማየት ከላይ የቀረበው አሳብ እንደመንደርደሪያን ሊያገለግል ይችላል፡፡
በአብዛኛው የአየር መንገድ ሠራተኞች በተለይ በአብራሪዎች እና በቴክኒሻኖች የሚነሳው ጥያቄ አስተዳደራዊ በደሎች ናቸው፡፡ እነዘህም ተመጣጣኝ የደሞዝ ክፍያ፣የሰራ እድገት እና የስራ ዝውውርን የሚመለከት ነው፡፡ ለምሳሌ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ውስጥ የሚሰራ ኢትዮጵያዊ አብራሪ የወር ደሞዙ ትልቁ 7 ሺህ ዶላር ሲሆን ( ይህ የገቢ ግብር ጭምር የሚያካትት ነው) ለውጭ አገራት ዜጎች ግን ላቅ እንደሚል ሠራተኞች ይናገራሉ፡፡ በእርግጥ በኢትዮጵያ የኑሮ ሁኔታ ሲታይ የብሩ መጠን ከፍተኛ ነው፡፡ ነገር ግን ክፍያው የሚፈፀመው የኢትዮጵያ አየር መንገዱ አለም አቀፍ እንደመሆኑ መጠን አለም አቀፍ ደረጃ በጠበቀ መልኩ ነው መሆን ያለበት፤ ለዚህም ነው ወራዊ ደሞዝ በብር ሳይሆን በዶላር የሚከፈለው፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ነው የአየር መንገድ ካፒቴኖች ለስራቸው ተመጣጣኝ ክፍያ እንዲከፈላቸው የሚጠይቁት፡፡
ይሁን እንጂ ሠራተኞች እንደሚናገሩት አስተዳደሩ ለጥያቂያቸው ተገቢ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ‹‹ስራውን መልቀቅ ትችላላችሁ›› ነው የሚባሉት፡፡ በዚህም ምክንያት ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ዋና እና ምክትል አብራሪዎች ከአገር በመውጣት በተለያየ አገር የሥራ ብቃታቸውን እያሳዩ ይገኛሉ፡፡ ነገሩን የበለጠ ግልፅ ለማድረግ እንዲረዳ ይህን መመልከት በቂ ይመስለኛል ባለፈው ሳምንት ተጠለፈ የተባለው ኤጥ 702 አውሮፕላን ዋና አብራሪ የነበሩት ግለሰብ ኣኢር እታሊአ (ኣል-እታኢአ) በተባለ የአየር መንገድ ድርጅት ውስጥ ሲያገለግሉ ቆይተው በውር 3 ሺህ ዶላር እየተከፈላቸው በጡረታ ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ እኚህ ግለሰብ በኢትዮጵያ አየር መንግድ ውስጥ 14 ሺህ ዶላር እየተከፈላቸው ይገኛል ፡፡
ሌላው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ አገራት ውስጥ ሎሜ፣ ቶጎ እና ማላዊ እንዲሁም በተቀሩት ማህከላዊ ምዕራብ አፍሪካ አገራት ውስጥ ባለው ከፍተኛ የሼር መጠን የሚያንቀሳቅሳቸው እና የሚያስተዳድራቸው የአየር መንገድ ድርጅቶች አሉ፡፡ በእነዚህ የአየር መንገድ ድርጅቶች ውስጥ በቴክኒሻንነት የሚያገለግሉ ማንኛው የውጪ አገር ዜጋ ከ 3 እስከ 5 ሺህ ዶላር ክፍያ ያገኛል፡፡ ነገር ግን ተመሳሳይ የት/ት እና የስራ ልምድ ያለው ኢትዮጵያዊ ቴክኒሻን የሚከፈለው 1 ሺህ ዶላር የማይሞላ ነው፡፡
በኢትዮጵያ አየር መንገድ ድርጅት ውስጥ ሌላው በሠራተኞች ዘንድ ትልቅ ቅሬታ ሆኖ የሚነሳው የስራ ዝውውር እና እድገት ግልፅነት እና ተጠያቂነት የሌለው መሆኑ ነው፡፡ወደ ተሻለ የስራ ቦታ ለመዘዋወር እና የደረጃ እድገት ለማግኘት በአብዛኛው በቅርብ አለቃ መላካም ፍቃድ ላይ የተመሰረተ እንጂ የሥራ ውጤትን ግብ ያደረገ አይደለም፡፡ ይህም ማለት በአየር መንገድ ድርጅት ውስጥ በሚኖሩ የስራ ክፍሎች በዋና ተጠሪነት የሚቀመጡት በአብዛኛው ለወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ቅርብ ከመሆናቸው በላይ ለስርአቱ ደም እና አጥንታቸውን የገበሩ ናቸው፡፡ ይህ መሆኑ ደግሞ ለሰራተኛ እድገት እና ዝውውር ዋንኛ መመዘኛ በማድረግ ተመልክተው ፍቃዳቸውን የሚሰጡት የሰራተኛው የስራ ልምድ እና የት/ት ዝግጅት በመመልከት ሳይሆን፣ ለወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ያለውን አመለካከት እና ጎሳን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ አብዛኛው የአየር መንገድ ሰራተኞች በድርጅታቸው ለሚታየው የአስተዳደር ችግሮች በቁጭት ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ የተቀሩት ደግሞ ሰራቸውን በመልቀቅ ከአገር ወጥተው ይገኛሉ፡፡
ይህ በእንዲ እንዳለ ከሰሞኑ ትልቅ አጀንዳ በመሆን መነጋገሪያ የሆነው የረዳት አብራሪ ሃይለመድህን አበራ የአውሮፕላን ጠለፋ ነው፡፡ የአውሮፕላን ጠለፋ ፖለቲካን መሰረት አድርጎ በአገራችን የተጀመረው ህዳር 29 ቀን 1965 ዓ.ም ሲሆን እነዋለልኝ መኮንን እና ማርታ መብራቱ ያካተተ ነበር፡፡የያኔው ጠላፋ ተሳክቶ ቢሆን ኖሮ ዋና አሳቡ ፖለቲካ ጥገኝነትን በመጠየቅ ከአገር ሸሽቱ ለመኖር ሳይሆን በጃንሆይ እና በአስተዳደራቸው ላይ ለተነሳው አመፅ የአውሮፕላን ጠለፋው የአመፁ የእስትራቴጂ አካል ጭምር ስለነበረ ነው፡፡
በእንዲ መልኩ የተጀመረው ፖለቲካዊ ይዘት ያለው የአውሮፕላን ጠለፋ በደርግ መንግስት ምን ያህል ተግባራዊ እንደሆን መረጃ ለማግኘት በእኔ በኩል ያልተቻለኝ ቢሆንም፤ ነገር ግን የአውሮፕላን ጠለፋ በቁጥር እና በአይነት በዝቶ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ጠለፋ የታየው በወያኔ/ኢህአዴግ የመንግስት የአስተዳደር ወቀት ስለመሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ እንዲሁም ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ የመንገደኛ እና የጦር አውሮፕላን ካፒቴኖች በተለያየ አገር የፖለቲካ ጥገኝነት ጠይቀው  በመኖር ላይ ይገኛሉ፡፡
በእርግጥ የእነዚህ ካፒቴኖች የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቅ በራሱ የእውነት ፖለቲካዊ ይዘት አለው ወይስ የለውም ለማለት ተገቢ የሆነ ጥናትና እውነታን የሚጠይቅ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ካፒቴን ተሾመ ተንኮሉ እና መስል አጋሮቹ በመንግስት ከደረሰባቸውን በደልና ግፍ በላይ በአገር ላይ የሚፈፀም በደል አላስችል ሲላቸው የፈፀሙት ገድል ሁሌም ታሪክ በበጎ የሚያስታውሰው ነው፡፡
ሌላው እና ለዚህ ጹሑፍ ዋንኛ መነሻ የሆነው አሳብ የረዳት አብራሪ ሃይለመድህን አበራ ጉዳይ ነው፡፡ እኔ ብቻ ሳልሆን ማንም ሰው በእርግጠኝነት ሊናገር የሚችለው አውሮፕላኑ ከአዲስ አበባ መነሳቱ እና ጄኔቫ ማረፉ ሲሆን፣ አውሮፕላኑ በጄኔቫ ያረፈው በታቀደው መልኩ ሳይሆን ከዚያ ውጪ በሆነ በረዳት አብራሪ ሃይለመድን አበራ ፍቃድ ብቻ መሆኑ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያሉ ነገሮች በአብዛኛው መላ ቅጡ በጠፋ መረጃ የተተበተበ ነው፡፡ በማህበራዊ ድረ-ገፅ እና በተለያዩ የዜና ማሰራጫዎች የሚነገሩ ነገሮች በአብዛኛው የወያኔ/ኢህአዴግ  መንግስት ደጋፊ፣ እንዲሁም ተቃዋሚም የሆን ሁሉ ዋንኛ መነሻ አሳባብ ከራስ ጥቅም እና ፍላጎት የመነጨ ነው፡፡ ይህም ስለመሆኑ የተነገሩት እና የተለቀቁትን መረጃዎች በማየት መገንዘብ ይቻላል፡፡
የነገሩን ውስብስብነት የበለጥ የሚያገላው ደግሞ የፓይለቱ ቤተሰቦች የሚሰጡት መረጃ ነው፡፡ ለማሳየነትም እንዲረዳ እህቱ ፣አክስቱ ፣ወንድሙ እንዲሁም የአጎቱ ባለቤት እና የቅርብ ጎደኛ በጉዳዩ ላይ የሚሰጡት ቃላቸው ፈፅሞ ሊቀራረብ የማይችል ነው፡፡ በተለይ ታላቅ ወንድሙ በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ባደረገው ቃለ መጠይቅ በአብዛኞቻቸን ዘንድ ሞቅ አድርግን ይሆናል ብለን በገመትነው ነገር ላይ ቀዝቃዛ ውሃ ነው የደፋበት፡፡
ይድነቃቸው ከበደ
ይድነቃቸው ከበደ
የረዳት ካፒቴን ሃይለመድን አበራ አውሮፕላኑን የጠለፈበት ምክንያት በእርግጠኝነት ልናውቅ የምንችለው ከራሱ በሚነገር እውነት ብቻ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ቀኑ የራቀ አይደለም ፤ስለዚህም ቀኑ ተጠብቁ ሙገሳውም ትችቱም ቢቀርብ ይበለጥ የተሻለ ይሆናል፡፡ እኔ በበኩሌ በዚህ ጉዳዩ ከመጀመሪያው ጀምሮ የያዝኩት አቋም ይህን ነው፡፡
የዚህ ጹሑፍ ማጠቃለያ የሚሆነው በኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚታዩ ችግሮች ዋንኛ ምክንያት የአስተዳደር የአቅም ውስንነት መሆኑ ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ቀጥተኛ የሆነ የመንግስት ጣልቃ ገብነት እና ብልሹ ፖለቲካዊ የአገር አስተዳደር ነው፡፡ በመሆኑም ሥራቸውን ብቻ በማየት በሥራቸው ለደረሰባቸው በደል አየር መንገዱን ለቀው ጥገኝነት የጠየቁ፡፡ እንዲሁም ከሚከፈላቸው ዶላር በላይ ስለአገራቸው እና ስለ ህዝብ ተቆርቁረው እንቢ ለሀገሬ ብለው ለተሰደዱ ለሁሉም ተጠያቂው በስልጣን ላይ ያለው የወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ነው፡፡
http://www.goolgule.com/ethiopian-airlines-and/

No comments:

Post a Comment