Saturday, March 8, 2014

ሰላማዊ ወይስ የትጥቅ ትግል ወይስ ማንፈራጠጥ

(ፕ/ር መስፍን ወልደ-ማርያም)

gun



የተማረ ወይም የእውቀት ባለቤት እንደሆነ የሚነገርለት የኢትዮጵያ ሕዝብ ክፍል ከወያኔ ጋር የሚደረገው ትግል ሰላማዊ ይሁን ወይስ በትጥቅ ትግል የሚለውን የጦፈ ክርክር ሲያደርግ ሃያ ሁለት ዓመታት ሆነው፤ ዳኛ የሌለበት ክርክር ስለሆነ የመደማመጥ ግዴታ ታይቶበት አይታወቅም፤ ስለዚህም በሁለቱ መሀከል ያለው ልዩነት ግልጽ ሆኖ አያውቅም፤
አንድ፣ ከሁሉ በፊት ሰላማዊ ትግል በሀሳብ ደረጃ መሆኑንና የትጥቅ ትግል ደግሞ በተግባር መሆኑን ለይቶ ለመረዳት ችግር ሆኖ ቆይቶኣል፤ በሌላ አነጋገር ሰላማዊ ትግል በሀሳብ፣ በንግግር፣ በተለያዩ ሀሳብን ለማስለወጥ መቀስቀሻ በሚሆኑ መንገዶች ተቃውሞን መግለጽ ነው፤ በአንጻሩ የትጥቅ ትግል በጠመንጃ ወይም በጉልበት ያለውን የአገዛዝ ሥርዓት ለመለወጥ የሚደረግ ሙከራ ነው፤
ሁለት፣ እንዲህ ከሆነ በሰላማዊ ትግል ለሚያምኑ ሰዎች ያለምንም ጥርጥር በተለያዩ ዓላማዎችና ዘዴዎች ላይ መከራከርና ሀሳብን ማጥራት አስፈላጊ ነው፤ በሰላማዊ ትግል ተግባር አለ ቢባልም በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የድጋፍ ወይም የተቃውሞ አቅዋሞችን ከማሳየት አያልፍም፤ አገዛዞች ጃዝ! ብለው ውሻና ፖሊስ በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ ሲለቁ የጉልበት ጥርስና ዱላ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ያርፋል፤ ጉዳት ይደርሳል፤ ሰላም ይቃወሳል፤ በሕዝብና በአገዛዙ መሀከል ቂም ይጀመራል።
ሦስት፣ የትጥቅ ትግል ደግሞ በተዋረድ በሚተላለፍ ትእዛዝ የሚፈጸም ግዴታ ነው፤ በትጥቅ ትግል ጉልበተኛ ከጉልበተኛ ጋር፣ ብረት ከብረት ጋር ይጋጠማል፤ የሰው ልጅ ለእርድ ይቀርባል፤ በሕይወታቸው በልተው ያልጠገቡ ምስኪኖች ለጥቂት ሰዎች የሥልጣን ጉጉት ይታረዳሉ፤ ያለቀባሪ በጅብና በአሞራ ይበላሉ፤ ዕድለኞች የሚባሉት እጆቻቸው፣ ወይም እግሮቻቸው ተቆርጠው፣ ወይም ዓይኖቻቸው ጠፍተው፣ ወይም ከዚህ ሁሉ የባሰ ጉዳት ደርሶባቸው በሕይወት የሚቀሩት ናቸው፤ ከነዚህ በሕይወት በቀሩት የጦር ጉዳተኞችና በጦርነቱ ላይ በሞቱት መሀከል የትኛው የተሻለ አንደሆነ የሞቱት ባይናገሩም ጉዳተኞቹ ይናገራሉ፤ ‹የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ!› እያሉ።
አራት፣ ሁለቱ የትግል ስልት ዓይነቶች በባሕርይ የተለዩ ናቸው፤ አንዱ ሌላውን የሚደግፍ አይደለም፤ ሰላማዊ ትግል የትጥቅ ትግልን ለመደገፍ ሰላማዊ የሚለውን ስያሜ መጣል አለበት፤ የትጥቅ ትግልም ሰላማዊ ትግልን ለመደገፍ ትጥቅ የሚለውን ስያሜ መተው አለበት፤ ሰላማዊ ትግልና የትጥቅ ትግል አራማጆች ድል ቢያደርጉ ማን ወንበሩ ላይ እንደሚወጣ ሳይታለም የተፈታ ነው፤ ጠመንጃ የያዘው ሥልጣኑን ሲይዝ ሰላማዊ ትግሉ ይቀጥላል! ያውም ከተፈቀደለት!
በኢትዮጵያ የቅርብ ጊዜ ታሪክ አርበኞች ሳይቀሩ በሩ ተዘግቶባቸው ለደጅ ጥናት እንደተዳረጉ አይተናል፤ መልኩን ለወጥ ቢያደርግም ደርግን ከተፋለሙት ውስጥ በአዲስ አበባና በአስመራ ወንበሮች ላይ ሲወጡ የተሸነፉት ወይ ለወያኔ ገብረው ሎሌነት ገቡ፤ ወይም በአሜሪካ መሽገው ያቅራራሉ፤ ዘመኑ እንዳለፈባቸውም ገና አልተረዱም።
አምስት፣ ሰላማዊ ትግልና የትጥቅ ትግል ሁለቱም ብርቱ ቃል ኪዳንን ይጠይቃሉ፤የቃል ኪዳናቸው ልዩነት አንዱ እስከሞት ለመታገል፣ ሌላው ደግሞ እስከመግደልና እስከመሞት ለመታገል መሆኑ ነው፤ ለሰላማዊው ትግል ከፍተኛ መንፈሳዊ ወኔ የሚያጎናጽፈው ለመግደል ያለው ተቃውሞ ነው፤ ሕይወትን ለማልማት ሕይወትን መቅጠፍ የአስተሳሰብም የመንፈስም ጉድፍ ያለበት ሥራ ነው።
የሰላማዊ ትግል ዋናውና ቀጥተኛው ተልእኮ ሕዝብን ለሥልጣን ባለቤትነት ማብቃት ነው፤ ሥልጣንን ለመያዝ አይደለም፤ ስለዚህም ኢላማው ሕዝብ ነው፤ በሥልጣን ወንበሩ ላይ ያሉት የሰላማዊ ትግሉን የሚቃወሙት በሕዝብ ዘንድ ተሰሚነትና ተቀባይነት እንዳያገኝ ለማድረግ ነው፤ ሰላማዊ ትግሉ የሚያተኩረው በሕዝቡ ጆሮ፣ አእምሮና ልብ ላይ ነው፤ አገዛዙ በበኩሉ ጸጥ-ለጥ ብሎ የሚገዛለት ሕዝብ እውቀቱ ዳብሮ፣ መብቶቹን ሁሉ ተገንዝቦ፣ በሕግ ለሕግ እንጂ ለሰው አልገዛም በማለት ልቡ እንዳይሸፍት አፈናውንና ማነቆውን በማጠናከር እያደነቆረ ለመግዛት ይፈልጋል፤ የሰብአዊ መብቶችን የሚያስተምሩና በአገዛዙ አካላት የሚፈጸሙትን የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችን የሚያጋልጡ ድርጅቶችን ማዳከም ወይም ማጥፋት ለአገዛዙ አስፈላጊ የሚሆነው ለዚህ ነው፤ ኢሳት የሚባለው የቴሌቪዥንና የራድዮ ፐሮግራም ለወያኔ የውስጥ እግር እሳት የሆነበት ለዚህ ነው፡፡ በሰውነት ደረጃ ሕዝቡ መብቶቹን ሁሉ እንዲያውቅና እንዲረዳ ማድረግ፣
በዜግነት ደረጃ ሕዝቡ ለሥልጣን የሚያበቃውን የዜግነትና የፖሊቲካ መብቶች እንዲያውቅና እንዲረዳ ማድረግ፣ ሕዝቡ የሰውነትና የዜግነት መብቶቹን ተገንዝቦ በአገዛዝ ስር አልተዳደርም የማለት መንፈሳዊ እምቢተኛነት እንዲያድርበት ማድረግ፣ በግልጽ ጭቆናን የሚጠላና ለመብቶቹና ለነጻነቱ በቆራጥነት የሚቆም ሕዝብ እንዲፈጠር ማበረታታት፣ መብቶቹንና የሥልጣን ባለቤትነቱን የተረዳና ከጭቆና ጋር የተጣላ ሕዝብ በፖሊቲካ መስመር ቡድኖችን እየፈጠረ እንዲደራጅ ማድረግ፣ ያወቀና የነቃ፣ በፖሊቲካ መስመር የተደራጀና ማናቸውንም ዓይነት ጭቆና የሚጠላ ሕዝብ ለማንም ጉልበተኛ የማይንበረከክ ሕዝባዊ ኃይል እንዲሆን መጣር፣
የትጥቅ ትግል ዋናውና ቀጥተኛው ተልእኮ በሥልጣን ላይ ያለውን አገዛዝ አውርዶ ወንበሩን ለራሱ ለመውሰድ ነው፤ ይህንን ሲያደርግ ሕዝቡን ወደጎን ትቶ ወይም ዘልሎ ነው፤ ነገር ግን አብዛኛውን ጊዜ በጠመንጃ ሥልጣን የሚይዙ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሥልጣኑን ለሕዝብ እናስረክባለን፤ ትክክለኛ ምርጫ እናካሂዳለን በማለት ሕዝቡን በተስፋና በጠመንጃ ይዞ ነው፤ ነገር ግን ሥልጣንን ሕዝብ ለፈቀደው አስረክበው ከቤተ መንግሥት ሲወጡ አናይም፤ ሲሸሹ ወይም ሬሳቸው ሲወጣ እንጂ።
ብዙውን ጊዜ የማይታሰብ ወይም ብዙዎች የሚዘነጉት የሁለቱ ትግሎች የገንዘብ ወጪ በጣም ከፍተኛ ልዩነት ያለው መሆኑን ነው፤ ሰላማዊ ትግል በሕይወትም፣ በንብረትም፣ በመሣሪያም በዝግጅትም የሚያስከፍለው ዋጋ ከትጥቅ ትግል ጋር ሲወዳደር በጣም አነስተኛ ነው።
ስለዚህም በሁለቱ በተለያዩ ስልቶች አራማጆች መሀከል የሚደረግ ክርክር ምን ዓይነት ነው? የሰላማዊው የመጀመሪያ ደረጃ ኢላማው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፤ የትጥቅ ትግል የመጀመሪያ ደረጃ ኢላማው የወያኔ አገዛዝ ነው፤ በሌላ አነጋገር በሰላማዊ ትግል ሕዝቡ በሰላማዊ ትግል ትንሽም ቢሆን የነጻነትን አድማስ ለማስፋት እንዲችል ድፍረትን በማስተማር በኩል የማይናቅ አስተዋጽኦ ቢያደርግም አገዛዙን የመነቅነቅ ኃይል ገና አላዳበረም፤ አንድም ውጤት አላሳየም፤ የትጥቅ ትግሉ ከፉከራና ከሽለላ እስካሁንም አልወጣም፤ የሰላማዊ ትግል ዓላማ ሕዝቡ መብቶቹን እንዲያውቅ ለማንቃትና ለመብቶቹ እንዲታገል የሚያስችለውን ብቃት ለማስጨበጥ ነው፤ ስለዚህም ዘዴው በሕዝቡ ላይ ነው፤ የትጥቅ ትግሉ ዘዴ አገዛዙን በጉልበት ገልብጦ በዚያው ባልተለወጠ ሕዝብ ላይ ሌላ አገዛዝ ለመመሥረት ነው።
በኢትዮጵያ ለውጥ እናመጣለን የሚሉ ሁሉ የቆሙበትንና የቆሙለትን ዓላማና ዘዴ በግልጽ ተገንዝበው ካልተሰለፉ በተንፈራጠጠ አስተሳሰብ የተባበረ ተግባር ሊገኝ አይችልም።
http://www.goolgule.com/non-violent-or-armed-struggle/

እነዚህ ሰዎች የሚናገሩትንም አያውቁም (ሲሳይ አባተ፣ ከአዲስ አበባ)

“ዘላለማዊ ክብርና ሞገስ ለትግሉ ሰማዕታት” (ጠቅላይ አሽከር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከደቂቃዎች በፊት የተናገረው)

ታጋይ አለማየሁ አቶምሳ
ጓድ አለማየሁ አቶምሳ
ለትግሉ መስዋእት የሆኑት ታጋይ አለማየሁ አቶምሳ
(የማን አስከሬን ተሸፍኖ የማን ሊገለጥ?)
የሕወሓት መንግሥት በአገዛዝ ዘመኑ ከተሳኩለት ነገሮች አንዱና ዋነኛው የቀብር ሥነ ሥርዓቶችን ባማረ ሁኔታ ማከናወን ነው፡፡ ባለፉት ዓመታት ከተከናወኑ የቀብር ሥነ ሥርዓቶች ውስጥ ለምሳሌ የሀየሎም አርአያ፣ የጭራቁ መለስ ዜናዊና የትዳር አፋቹ የወንበዴው ጳጳስ የጳውሎስ ደማቅ የልቅሶና የቀብር ሥነ ሥርዓቶች በዋቢነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ የጥላሁን ገሠሠን ያላካተትኩት የሕዝብና የሀገር ልቅሶና ሀዘን ስለነበረ ነው፡፡ እንጂ በሀገር ደረጃ ካየነው የጥላሁንን የመሰለ ደማቅ ልባዊ ሀዘን የተገለጸበት ልቅሶ ታይቶ የሚታወቅ አይመስለኝም፡፡ በጥላሁን ቀብር ሕዝብ በዐዋጅና በማባበያ ወጥቶ እንዲለቀስ አልተደረገም፡፡ በጥላሁን ቀብር የሀገር ሀብት ከካዝና እየተመዘረጠ ከናቴራና ኮፍያ እየተገዛ ፖስተርም እየተለጠፈ፣ የውሎ አበልም እየተከፈለ በመቶ ሚሊዮኖች የሚገመት ገንዘብና ማቴሪያል እንዲባክን አልተደረገም፡፡ በጥላሁን ቀብር ሕዝብ በግዳጅ እንዲያለቅስና ከሥራ እየቀረ ከአንጀቱ ሳይሆን ከአንገቱ እንዲያላዝን አልተደረገም፡፡ የሰሜን ኮርያን ልቅሶ የሚያስንቅ የግዳጅ ልቅሶ ያዬነው በመለስ ዜናዊ ቀብር ነው – በሀፍረት የለሹ ወያኔ አስገዳጅነት፡፡Former president of the Oromia region, Ato Alemayehu Atomsa
ዛሬ ደግሞ ግራ የተጋባ ልቅሶ እያየን ነው፡፡ የሰዎች መሞት በውነቱ ያሳዝናል፡፡ አቶ አለማየሁ አቶምሳ ሞቷል – በሰውነቱ ከልብ እናዝናለን፡፡ በሆዳምነቱና ከታሪካዊ ጠላቶቹ ጋር ተባብሮ ለሀገር መቀበር በመታገሉም እንዲሁ እናዝንበታለን፤ ለማንኛውም ፈጣሪ ነፍሱን ይማር – አፈሩንም ገለባ ያድርግለት፡፡ ለልጆቹና መላ ቤተሰቡ አጽናኝ መላእክትን ይዘዝላቸው፡፡ በመሠረቱ ሰውዬው የሞተው ዛሬ አይደለም፡፡ የሞተው የዛሬ ሦስት ዓመት ገደማ ናዝሬት ውስጥ ታካሄደ በተባለ የኦህዴድ ጉባኤ ላይ ጓደኞቹ ይሁኑ ሌላ ወገን በሚጠጣው ይሁን በሚበላው ነገር ላይ መርዝ በሰጡት ጊዜ ነው፡፡ ወያኔ ራሱ ገድሎ  ሙሾ ማውረድን የተካነበት በመሆኑ ራሱ የገደለውን አለማየሁ በድምቀት እየሸኘው ነው፡፡ ዕንቆቅልሹ ወያኔ ክንፈ የሚባለውን የደህንነት ኃላፊውን ባስገደለበት ወቅት እንዴት በመሰለ ሁኔታ ቁንጮው ጭራቅ መለስ እያለቀሰ እንደሸኘው የምናስታውሰው ነው፡፡ እስስቶች ናቸው፡፡
የዛሬው ግራ አጋቢ የልቅሶ ሥነ ሥርዓት ምን ይመስላል? ሬሣው በዓለም እንደሚታወቀው ከአንገቱ በላይ እንዲታይ አልተደረገም፡፡ በኔ ግምት ይህ ያልሆነበት ምክንያት የፈራረሰው የመለስ አስከሬን ተሸፍኖ እንደተሸኘ ሁሉ ይህንንም ሰውዬ የእርሱ መናጆ በማድረግ የመለስ አስከሬን ሁኔታ እንዳይታወስና መነጋገሪያ እንዳይሆን ነው፡፡ አስከሬንን አለማሳየት ባህላቸው ነው እንዲባልና የመለስን መፈራረስ ለማስረሳት የፈለጉ ይመስለኛል፡፡ እንጂ የአለማየሁ ሰውነት እንደመለስ የፈራረስ አይመስለኝም፡፡ አንደኛ ነገር ይህ ሰው የሞተው ሰሞኑን ስብሰባ እያካሄደ በነበረበት ጊዜ ድንገት ተስለምልሞ በመውደቅና ከዚያም ወዲያውኑ ወደውጪ ተልኮ የህክምና ርዳታ ተደርጎለት ነው፡፡ ስለዚህ ጭንቅላቱም ሆነ ፊቱ ገና ‹ፍረሽ› ነው፡፡ ሁለተኛ ከሞተም በኋላ እንደመለስ ለወራት አልተደበቀም፤ የተፋጠነ የቀብር ሥነ ሥርዓት ነው እየተደረገለት ያለው፡፡ በዚህች በቀብር ሥርዓት እንኳን ከሕወሓት ውጪ ያሉ ሌሎች ወገኖች መወሰን አልቻሉም ማለት ነው፡፡
ይህ ሀዘን ክልላዊ እንጂ ፌዴራላዊ አይደለም፡፡ የፕሮቶኮል ጉዳይ ያነጋግራል፡፡ ባንዴራ ዝቅ ተደርጎ መውለብለብ ያለበት ሰውዬው ይመራው ነበር በሚባለው “ክልላዊ መንግሥት” እንጂ በመላዋ ኢትዮጵያ መሆን አልነበረበትም፡፡ ስህተት ነው፡፡ አወሳሰኑ ራሱም ስህተት ነው፡፡ አንድ ግለሰብ ወይም የጥቂት ግለሰቦች ውሳኔ ይመስላል፡፡ የተሰበሰበ የፓርላማ ጉባኤ ሳይኖር ጥቂት ሽፍቶች እንደፈለጉ የሚያዙበትና የሚናዝዙበት መንግሥት ያለን ለመሆናችን አንደኛው ዋቢ ነው፡፡ ለማስመሰልም እንኳን አልቻሉበትም፡፡ ለወትሮው የማስመሰል ሁኔታ ይታይ ነበር፤ የዐይን ጥቅሻ ብቻ እያዬ የሚያጨበጭብና በረጃጅም ዲስኩሮች ወቅት ደግሞ እያዛጋና እያንጎላጀ እንቅልፉን የሚለጥጥ ፓርላማ ያለን እኛ ብቻ ነን – ዕድሜ ለወያኔ፡፡ አሁን አሁን የነበረው ጥቂት የማስመሰል ትያትር በጭራሽ ጠፍቷል፡፡ ከአንድ ጎሬ ውስጥ የተደበቀ ሥውር መንግሥት ሳይኖር አይቀርም፡፡ ያ ሥውር ወያኔዊ ኃይል የመንግሥት ወንበሮች ላይ በጎለታቸው እነኃይለማርያምንና ተሾመን የመሳሰሉ ሆዳሞች አማካይነት በስልክ በሚተላለፍ ቀጥተኛ ትዕዛዝ ሀገሪቱን እንደፈለገ መንዳቱን ቀጥሏል፡፡
ሬሣው መልበስ ያለበት የክልሉን ባንዴራ መሆን ሲገባው በአንድ በኩል የወያኔን የኢትዮጵያ ባዴራ አልብሰው በሌላ በኩል ደግሞ ኦሮምያ የሚባለውን አዲስ ወያኔ ሠራሽ ሀገር ባንዴራ አልብሰውታል፡፡ አስከሬኑ የሚመስለው አስከሬን ሳይሆን  የተለያዩ ቀለማት ባላቸው ጨርቃ ጨርቆች ያሸበረቀ የጠንቋይ ቤት የመጠንቆያ ክፍል ነው፡፡ ቋንቋቸው ደግሞ የበለጠ ግራ ያጋባል፡፡
እነዚህ ሰዎች የቃላት አጠቃቀማቸው ራሱ አስገራሚ ነው፡፡ ጭራቁ መለስ ሲሞት ደደቧ ሚስቱ “መለስ ተሰዋ” ብላ በሀዘናችን መሃል አሳቀችን፡፡ አንድ ሰው ተሰዋ የሚባለው በጦርነት ላይ ሲሞት ወይም ለግዳጅ በሄደበት ሳይመለስ ሲቀርና ሕይወቱ በዚያው ሲያልፍ ነው፡፡ እንጂ በሰላም ሀገር ታሞ የሞተን ሰው ተሰዋ ማለት የቋንቋ ችግርን ከማሳየቱ በስተቀር ሌላ ትርጉም የለውም፡፡ በውነቱ ማይምነት ነው፡፡ በሌላ ወገንም የመንግሥት ሥልጣን ከያዙ ከ23 ዓመታት በኋላ “ታጋይ” እያሉ ሰዎቻቸውን ሲጠሩ ስንሰማ ምን ማለት እንደፈለጉ አይገባንምና መቸገራችን አይቀርም፡፡ ታጋይ የሚባለው በትግል ወቅት ነው፡፡ አሁን ባለሥልጣን ሊያውም የአሜባን ቅርፅ ይዞ ከኤርትራ በስተቀር በመላዋ ኢትዮጵያ እዚያና እዚህ ጉች ጉች ያለ የተንጣለለ የኦሮሚያን ክልላዊ መንግሥት “ከነሙሉ ክብሩና ማዕረጉ በነፃነት ሲያስተዳድር” የነበረ ዕንቁ ዜጋ! አይ ወያኔ፡፡ ስንቱን ነው እያሳየን የሚገኘው፡፡ ይብላኝልህ አንተ ታሪክ የምትባል ሀገራዊ ደደብ መዝገብ፡፡ ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ሀገር ከነዚህ መዥገሮችና ነቀዞች ነፃ ስትወጣ ሀፍረትህ ምንኛ የበረታ ይሆን?
ደንቆሮው ኃይለማርያም ደግሞ ያሳዝነኛል፡፡ የተሰጠውን እንዳነበበ “የሥልጣን ጊዜው”ን ሊጨርስ ነው፡፡ ምን ዓይነቱ ገልቱ ሰው ነው? እሱም ዛሬ ልክ እንደዚያች የመርገምት ፍሬ እንደአዜብ ጎላ አለማየሁን ‹መስዋእት የሆነ ታጋይ› ብሎት ዐረፈው፡፡ የት ዐውደ ውጊያ ሲፋለም ይሆን አቶ አለማየሁ የተሰዋው? በዚህ ብቻም አላበቃም፡፡ ለመለስ የተናገረውን ትንሽ ለወጥ አድርገው ጽፈው ሰጡትና “ዘላለማዊ ክብርና ሞገስ ለሰማዕታት” ብሎ ተናገረ፤ አለማየሁም ሰማዕት መሆኑ ነው (ሰማዕት የሚባለውንም ቃል ከሃይማኖታዊው ዐውድ አውጥተን ለዓለማዊ ፍጆታ ካዋልነው በትግል ወቅት የተሰዋ ማለት እንጂ በአገር አማን በበሽታ የሚነጠቅን ዜጋ ለማመልከት አይደለም)፡፡ ለውጡ በፊተኛው ጊዜ ይህን መፈክር የተናገረው ለመለስ ነበር፡፡ አሁን ግን ለሞቱትና ለመሞት ለተዘጋጁት ለነሳሞራና ሥዩም እንዲሁም ለሌሎቹም ተራቸውን እየተጠባበቁ ላሉ ሟቾች ጭምር ነው፡፡ የወደፊቱ ጊዜ የወያኔዎች መረፍረፊያ ጊዜ ነው፡፡ (ኢቲቪን አሁን ስመለከት ካህናት ጸሎተ ፍትሃት እያደረጉ ነው፡፡ የታደሉ ወያኔዎች ናቸው ጃል! ቤተ ክርስቲያንን ሲፈልጉ ያጠፏታል ሲፈልጉም የማስመሰያ  ፍትሃት እንድታደርግላቸው ያስደርጓታል፤ ሁሉ በጃቸው ሁሉ በደጃቸው – ማን ሃይ ሊላቸው፡፡ አለማየሁ እየተፈታ ነው፤ ሊያውም ከስንት አድባራት በልዩ ትዕዛዝ በተጠሩ ጳጳሳትና ካህናት፡፡ ይሄኔ ተቃዋሚ ቢሞት ኖሮ መንግሥትም ቤተ ክርስቲያንም ያን የሞተ ሰው እንደሥጋት በመቁጠር የውሻ ያህልም ክብር ባልሰጡት፡፡ ምን ዓይነት ቤተ ክርስቲያንና ምን ዓይነት መንግሥት ናቸው ያሉን? ያሉ የሚመስሉ ግን የሌሉ፡፡ ለሞተም የሚያዳሉና ሙታንንም የሚከፋፍሉ አስገራሚ ጉዶች!)…
ብዕር ካነሳሁ አይቀር በእግረ መንገድ አንድ ሌላ ጉዳይ ላንሳ መሰለኝ፡፡ ፕሮፌሰር መስፍንን ምን እየነካቸው ነው? ትናንት አንድ መጣጥፋቸውን ከዘሀበሻ ድረገፅ ላይ አነበብኩ፡፡ ጽሑፋቸው ቆንጆ ነው፡፡ እንደሁልጊዜው ሁሉ በፍቅር ነው ያነበብኩት፡፡ ነገር ግን አንዳንዴ አዝንባቸዋለሁ፡፡ ግራ የገባቸውም ይመስለኛል፡፡ ግራ ተጋብተውም እኔንም ግራ ያጋቡኛል፡፡ ምን ያለ ግራ አጋቢ ዘመን ላይ ደረስን እባካችሁ!
ግንቦት ሰባትን ለምን ትኩር ጥምድ አድርገው እንደያዙት አልገባህ ብሎኛል፡፡ እርሳቸው እደግፋዋለሁ በሚሉት ሰላማዊ የትግል ሥልት የኢትዮጵያን ሕዝብ ነፃ ማውጣት እንደማይቻል የተረዱ አልመሰለኝም፡፡ የትጥቅ ትግልን እንዳናናቁና ሕዝቡ ለባርነት እንደተጋለጠ በሰልፍና በወረቀት ላይ ብቻ ተወስኖ እየተጯጯኸ ዕድሜውን እንዲጨረስ ይፈልጋሉ መሰለኝ፡፡ ምን ማለታቸው ነው? “ያውጡብሽ እምቢ፤ ያግቡብሽ እምቢ” ይባላል እንደዚህ ያለ የማይፈታ ዕንቆቅልሽ ሲገጥም፡፡
መካሪ ማጣት ነው፡፡ ወይም ሰውን መናቅ ነው፡፡ እንደ አካሄድ ትልቅነት ጥሩ ነው፡፡ አባትነት መልካም ነው፡፡ ታዋቂነት ደግ ነው፡፡ መማር መመራመር ውብ ነው፡፡ በሥራ ጉዳይ ሀገርን ተዟዙሮ መቃኘትና ለትውልድ የሚተርፍ ምሁራዊ ትሩፋት ማስገኘት ብዙዎች ተመኝተው የማያገኙት መታደል ነው፡፡ በነዚህ ሁሉ ፕሮፌሰሩን አከብራለሁ፤ እወዳቸውማለሁ፡፡ ብዙዎች ወገኖቼ እንደሚቸሯቸው ያለ እውነተኛ ፍቅር እኔም ለእኚህ ሀገራዊ ቅርስ አባት አለኝ፡፡ ይሁንና ተሰሚነታቸውን በመጠቀም ለሀገር አንዳች ነገር እንሠራለን ብለው ገንዘባቸውን፣ ዕድሜያቸውን፣ ጊዜያቸውንና መላ ትኩረታቸውን የሚያውሉ ወገኖችን ማወክ ተገቢና ወቅታዊም አልመስለኝም፡፡ አንገት የተፈጠረው አዙሮ ለማየት ነው፡፡ አዙሮ ማየት ደግሞ በትልቅና በትንሽ ስብዕና የሚወሰን አይደለም፡፡ ስህተትን መሥራት በሰውነት ደረጃ የሚገታ እንዳልሆነ ሁሉ ከስህተት ጎዳና ለመውጣት መጣርና ራስን ለመፈተሸ ጊዜና አቅል መግዛትም ለተወሰኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች ብቻ የሚተው አይደለም፡፡ እናም ክቡር ፕሮፌሰር ነገሬን በጥሞና እንደሚረዱልኝ እገምታለሁ፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ያለበትን ሁኔታ የተገነዘቡ አልመሰለኝም፡፡ እርሳቸው በፋክት መጽሔት የፈለጉትን ስለተነፈሱና በጡረታም ሆነ በሌላ መንገድ በሚያገኙት (መጠነኛ) ገንዘብ ሕይወታቸውን ከብዙዎች ዜጎች በተሻለ ሁኔታ ስለመሩ ሕዝቡ ተመችቶታል ብለው የሚያስቡ ከሆነ ተሳስተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያለበትን የባርነት ሰቆቃ መረዳት አለባቸው፡፡ ችግሩ የአምባገነንነትና የዴሞክራሲ ጉዳይ አይደለም፡፡ በነፕሮፌሰር ቀለል ተደርጎ እንደሚገለጠው የዴሞክራሲ ዕጦትና የአምባገነን መንግሥት ጉዳይ የሀገራችን አንገብጋቢ ችግር አይደለም፡፡ ይሄን መሰሉ የነፕሮፌሰር ገለጣ ቅንጦት ነው – እዬዬም ሲደላ ነው ወገኖቼ፡፡ የኛ ችግር በነፃነትና በባርነት መካከል የሚዋልል የጠበበ አማራጭ ነው፡፡ ነፃነቱ ከተገኘ በኋላ ስለአምባገነን መንግሥትም ሆነ ግለሰቦች መነጋገር ይቻላል፡፡ አሁን ግን በአፓርታይድና በቅኝ ግዛት ውስጥ በመከራ ሥጋ በመከራ ነፍስ ውስጥ ተጣብቀው እየኖሩ ስለወደፊት አምባገነን ሥርዓት መነጋገር በትንሹ ቂልነት ነው፡፡ አለፍ ሲልም ዕብደትና ወፈፌነት ነው፡፡ አሁን በሌለ ሥልጣን፣ ባልተገኘ ምቹ ሀገራዊ የሥልጣን አያያዝ ሁኔታ ገና ለገና ግንቦት ሰባት ሥልጣን ይይዝና ጭቆናን ያራምድ ይሆናል ብሎ ሕዝብን ማደናገርና ማደናበር ከሀበሻዊ የምቀኝነት አባዜ ነጻ አለመውጣትን እንጂ ቀናነትን የተላበሰ ሀገራዊ መቆርቆርን አያመለክትም – It is really a far-fetched and more of imaginary concern for the time being. ትግላችን ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው አቢይ ትኩረት  ይህን በስብሶ ያበሰበሰንንና ተረካቢ ትውልድ ሳይቀር እንዳይኖረን እያደረገን የሚገኘውን የዘረኝነት ሥርዓት አስወግደን ቢያንስ ቢንስ ሁላችንንም በእኩል የሚጨቁን ወይም በእኩል የሚገድል ሥርዓት ማምጣት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ያለው ትግል ቀላል ነው፡፡ የራሳችንን ጨቋኞች ካገኘን በኋላ ወደ ዴሞክራሲ የሚደረገው ጉዜ በግማሽ አጠረ እንደማለት ነው፡፡ አሁን ግን በቅዠት ዓለም እየዋኙ እንደዶክኪሾት በምናብም በእውንም ከሚያስቡትና ከሚያገኙት “ጠላት” ጋር መላተም የህመም ካልሆነ የጤና ሊሆን አይችልም፡፡ ያስተዛዝባልም፡፡ እንዴ፤ ልብ እንግዛ እንጂ፡፡ እስከመቼ አንድ ዓይነት አንቺ ሆዬ ቅኝት እንዘፍናለን? “ሦስተኛውን” ዐይናችንን እንግለጥ፡፡
አንዲት ሴት እንዲህ አለች አሉ – ለባሏ፡፡ “ስንደዶ ቀጭቼ፣ አከርማ ቆረጬ ወስከምቢያ ሰፍቼ እሸጥና አንዲት ላም እገዛለሁ፡፡ ላሚቱን አስጠቅቼ አርግዛ ስትወልድ ጥጃዋን እዚያች እግገኗ ላይ አስራታለሁ፡፡” ሞኙ ባል ደግሞ “የለም፣ የለም፤ ምን ማለትሽ ነው? እግገኑ ላይማ አናስርም፤ ሰው ይገባል ይወጣል፡፡ የሰው ዐይን ደግሞ እንኳንስ ጥጃ ድንጋይ ይሰብራል፡፡ ስለዚህ ጓዳ ውስጥ እንጂ እዚህ አናስራትም፡፡”  ሚስትዮዋም ቀጠለች፡- “ምን ማለትህ ነው፤ ጓዳ ውስጥማ አናስርም፤ እዚሁ ነው የምናስራት፡፡ ደግሞስ አንተን ምን ጥልቅ አደረገህ? ለፍቼ ደክሜ ላሟን እምገዛና አሰጠቅቼ ጥጃዋን እማስወልድ እኔ፡፡ …” ክርክሩ ጦፈ፤ ወደ ከፍተኛ ግጭትም አመራና ባልዮው አጠገቡ የነበረ የቡና ዘነዘና አንስቶ አናቷን በርቅሶ ገደላት – ነፍሷን ይማር፡፡ ይታያችሁ – በላም አለኝ በሰማይ ምኑም ምኑም በሌለበት ሁኔታ በባዶ ሜዳ ተጨቃጨቁና ተገዳደሉ፡፡ የብዙ ሰዎች ችግር ይህን ይመስላል፡፡ የሌለ ሥጋት እየፈጠሩ በማውራትና በማስወራት ከፊት ለፊት የተጋረጠብንን ትልቅ ተራራና አለት በጋራና በቻልነው መንገድ ሁሉ ገፍተን እንዳንጥል ደንቃራ እየሆኑብን ነው፡፡ የሚሆነው ሁሉ ከመሆን ባይዘልም እነዚህን መሰል የ“ሳይቸግር ጤፍ ብድር” ዜጎች ወደየኅሊናቸው እንዲመለሱ እንጸልይ፡፡ እንቅፋትነታቸው ግልጽ ነውና፡፡
ግንቦት ሰባት ስህተት ሊሠራ ይችላል፤ “እንከን የለሽ ነው፡፡ ምሉዕ በኩልሄም ነው” የሚል እምነትም ሆነ አስተሳሰብ የለኝም – በሰዎች ስለሰዎች የሚመራ በመሆኑ ፍጹም ነው ማት አንችልም፡፡ ግን ከስህተታቸው እየተማሩ ወደ መልም ዘለቄታ የሚያመሩ ይመስሉኛል፡፡ (አንዲት ቀልድ ቢጤ ጣል ላድርግ፤ አንድ ሰው የሚጋልበው ፈረስ ዐመለኛ ኖሮ ተቸግሯል፡፡ አልታዘዝለት ብሎ ገደል ሊከተው ደረሰ፡፡ ተመልካቾችም አንዳቸው “አንገቱን ያዘው”፣ ሌላኛቸው ልጓሙን ጨብጠው” ደግሞም ሌላኛቸው “እርካቡን እርገጠው” ወዘተ. ሲሉ የሰማቸው ችግር ውስጥ የሚገኝ ሰውዬ “አይ መሬት ያለ ሰው!” አለ አይባላል፡፡ ልክ ነው – ያልተነካ ግልግል እንዳለማወቁ ቁጭ ብሎ ወሬ የሚጠርቅ የኔ ዓይነቱ ሥራ ፈት ሰው የሚለው አያጣምና ብዙ ሊፈላሰፍ በዚያ ፍልስፍናውም ብዙ ሊሳሳት ይችላል፡፡ ተሳስቶ ከማሳሳት ይሰውረን ወገኖቼ፡፡) በመሠረቱ እኔ የግንቦት ሰባት አባልም ሆነ አቦካቶው አይደለሁም፡፡ ግን አዳሜ እየተነሣ የጭቃ ጅራፉን ሲለጥፍበት ያሳዝነኛል – ብዙ የምታዘበው ነገር ስላለ ነው እንደዚህ በምሬት የምናገረው፡፡ በእውነቱ የማንሠራና የማናሠራ ዜጎች ብዙ ነን፡፡ ባሕርያችን ለያዥ ለገራዥ የሚያስቸግር ክርት ዐመል ያለን ብዙ ነን፤ ምን እንደሚሻለን አላውቅም፡፡ አለቃ ገ/ሃና “ለቦና ጥጃ ውስ ምን አነሰው” አሉ አሉ፡፡ እናስ ስንትና ስንት የሚወራበትና የሚጨነቁለት ችግር እያለ አሁን በምትወዱት ሞት ይሁንባችሁና ግንቦት ሰባት ለኢትዮጵያ ከወያኔ የበለጠ ራስ ምታት ሆኖ ነው ይህን ያህል ሰዎች እንቅልፍ አጥተውለት ከወያኔ ባልተናነሰ ለውድመቱ የሚቋምጡለት? ከማንም ጋር ይሥራ – የሚያዋጣውን የሚያውቅ ራሱ ነው፡፡ ስህተቱን መጠቆም፣ ማረም፣ ማስተማር፣ ማስተካከልና በተቻለ አቅም ሁሉ መርዳት ሲገባ ቤተስኪያን እንደገባች ውሻ ችው ችው ማለት ከአንድ ጤናማ ኢትዮጵያዊ ዜጋ አይጠበቅም፤ ሁል ጊዜ በምቀኝነት አባዜ መጠመድም ተገቢ አይደለም፡፡ ትንሽዬ ዝናና ስመጥርነት ስላገኘ ብቻ ባለን የቆዬ የምቀኝነት ባህል እየታወርን ሳቢን ለመግረፍ መጣደፍ አግባብ አይደለምና አንዳንዶቻችን ከምንጓዝበት እርምጥምጥ መንገድ በአፋጣኝ እንውጣ፡፡ ቢያንስ ዝም እንበል – ቆርጠን እየቀጠልን በምንፈጥራቸው ስድቦች ሰድበን ለሰዳቢ አንስጠው – “የምታሸንፈውን ምታ” ቢሉት ወደ ሚስቱ እንደሮጠው ፈሪ ባል ወያኔ ሲያቅተን በዚህ የትናንት ድርጅት አንረባረብ፤ ባይሆን ወፌ ቆመች እንበለውና የበኩሉን እንዲጥር እናግዘው፡፡ ከፈራነውም አሁኑኑ በእማኞች ፊት እናስፈርመውና ሥልጣኑን ከወያኔ እንደቀማ – ህልሙ ተሳክቶለት መቀማት ከቻለ – ሕዝብ ለሚመርጠው ሰው እንዲያስረክብ ቃል እናስገባው፡፡ በበኩሌ ምነው ግንቦት ሰባት በተሳካለትና በኢትዮጵያዊ አምባገነን በተገዛሁ እላለሁ፡፡ የራሴን አምባገነን መታገል እመርጣለሁ በባርነት የአፓርታይድ ሥርዓት ውስጥ ከሰውነት በታች ሆኜ ከምኖር፡፡ የምርጫ ጉዳይ ነው፡፡ ግንቦት ሰባት በሁኔታዎች አስገዳጅነት ሊሠራቸው በሚችላቸው ስህተቶች ምክንያት በጭካኔና በኢዴሞክራሲያዊነት ከወያኔ ጋር መፈረጅ የጤና አይመስለኝም፡፡ በእግረ መንገድም ኢሳትን ከግንቦት ሰባት ጋር እያያያዙ ይህን የሕዝብ ብሶት መተንፈሻ ጣቢያ እንዲጠላ የማድረግ ዘመቻ አሁኑኑ ማቆም የሚገባ ይመስለኛል፡፡ ኢሳትን ሲዘልፉትና ሲሰድቡት ስሰማ እነዚህ ሰዎች በተጠናወታቸው ሥነ ልቦናዊ ደዌ አዝናለሁ፡፡ ከወያኔ ምንዳ ተቀብለው ይሆን ብዬም ለማሰብ እገደዳለሁ፡፡ ኢትዮጵያውያን እንደዚህ ዘመን ክፉኛ የተከፋፈልንበትና በጦዘ የርስ በርስ ቅራኔ የገባንበት ዘመን ይኖር ይሆን? ለማንኛውም ስንናገርና ስንጽፍ ከአንዴ በላይ አሰብ እያደረግን ቢሆን መልካም ነው፡፡ ወደ ቀብር ልሄድ ነው –  ቻዎ፡፡
http://ecadforum.com/Amharic/archives/11343/